Feb 7, 2014

ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ለኢትዮጵያ ጥናታዊ ጽሁፍ - ተክሉ አባተ

 ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ለኢትዮጵያ: ጥናታዊ ጽሁፍ


 ተክሉ አባተ
በአገራችን ኢትዮጵያ ያለውን ብሄር ገነን ሥርዓት በእውነተኛ ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር ለመተካት ኢትዮጵያውያን (የ አገር ዜግነት ያላቸውን ትውልደ ኢትዮጵያውያንንም ማለቴ ነው) የተለያዩ  መንገዶችንና ዘዴዎችን በመጠቀም እየታገሉ ይገኛሉ:: በአገር ቤት ያሉ ወደ 100 የሚጠጉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በይፋ ሰላማዊ የትግል ስልት ይከተላሉ ቀላል የማይባል ህዝብም በሰላማዊ መንገድ መታገል እንደሚበጅ ያምናል:: በጣት የሚቆጠሩ ድርጅቶች ደግሞ እሾህን በእሾህ እንዲሉ መሳርያ አንስተው ወደበረሃ ገብተዋል:: እንደ ግንቦት 7 ያሉት ደግሞ ሁሉንም አይነት የትግል ስልት መጠቀም አዋጭ እንደሆነ ያምናሉ::

በአንድም በሌላም መንገድ ስለነዚህ የትግል ስልቶች አንጻራዊ አዋጭነትና አስፈላጊነት ውይይቶች ሲደረጉ ነበር:: ነገር ግን የትኛው የትግል ስልት ትክክለኛ ለውጥ ለማምጣት አስተማማኝ እንደሆነ መደምደም የሚቻል አይመስልም:: ለዚህም ይመስላል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማኅበራዊ ሚዲያዎችና በድረ ገጾች የሚደረጉ ውይይቶችና የሚለቀቁ መጣጥፎች ይህን ጉዳይ በቀጥታ የማያነሱት::

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በርከት ያሉ ውይይቶችና መጣጥፎች እያተኮሩበት የመጣው ጉዳይ ትንሽ የተለዬ ይመስላል:: ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ማድረግ ለአገራችን ሰላማዊና ዘለቄታዊ ለውጥ ማምጣት እንደሚችል እየተነገረ ነው:: ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ማድረግ ከባህላችን ጋር አብሮ ከመሄዱም በላይ እጅግ አስፈላጊና ወቅታዊም እንደሆነ የሚሞግቱ አሉ:: በአንጻሩ ደግሞ ብሄራዊ እርቅ ፈጽሞ የማይሰራ ከመሆኑም በላይ የህግንና ፍትህን መርሆች የሚቃወም እንደሆነ የሚያስጠነቅቁም አሉ:: አንዳንዶች ደግሞ ስለብሄራዊ መግባባትና እርቅ ማውራትና መወያየት የዋህነት አላዋቂነት ሃይማኖታዊነት እንደሆነ በድፍረት ይናገራሉ:: ሌሎች ደግሞ ሃሳቡ መንግስትና ባለሥልጣናቱን ለመታደግ የታሰበ የቆረጣ ስልት እንደሆ ይጠቁማሉ::

ዳሩ ግን ብሄራዊ ኢትዮጵያዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ ጠቅለል ያለ የዳሰሳ ጥናት እስካሁን አልቀረበም:: ጉዳዩን በተመለከተ የሚደረጉት የተናጥል ውይይቶችና የተጻፉት መጣጥፎች የተሟላ ሃሳብ ለማግኘት አያስችሉም:: እንዲያውም በጉዳዩ ላይ ምን ያህል እንደተጻፈና ምን ምን ዝርዝር ሃሳቦች እንደተነሱ አይታወቅም:: ይህም ብሄራዊ መግባባትና እርቅ በይፋ እንደ አንድ የትግል ስልት እንዳይቆጠርና በጽንሰ ሃሳብ ደረጃ ዳብሮ ሥራ ላይ እንዳይውል ተጽእኖ  አሳድሯል:: ይህን ችግር ለመቅረፍ የዳሰሳ ጥናት አስፈላጊ ሆኗል:: የዚህ ጥናታዊ ጽሁፍ ዓላማ ጉዳዩን በተመለከተ የተጻፉትን መሠረት በማድረግ አጠቃላይ ግንዛቤ እንዲኖርና በርዕሱ ላይ ውይይት ተጠናክሮ  እንዲቀጥል ማነሳሳት ነው::   

የጥናቱ ዓላማ

የዚህ ጥናት ዋና ዋና ዓላማዎች ቀጥለው የተዘረዘሩት ናቸው:: 
1.      እስካሁን ድረስ ስለብሄራዊ (ኢትዮጵያዊ) መግባባትና እርቅ  በጽንሰ ሃሳብ ደረጃ ምን እንደተጻፈ መመርመር  
2.     ብሄራዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ በሚገባ ያልተብራሩ ሃሳቦችን ለይቶ ማውጣት
3.     ብሄራዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ ወደፊት በጽንሰ ሃሳብና በተግባር ደረጃ ምን መደረግ እንዳለበት መጠቆም


የጥናቱ ዘዴና የመረጃ ምንጮች

በእርግጥ በድረ ገጾች በፌስቡክ በፓልቶክ ክፍሎች እንዲሁም በቴሌቪዥንና በሬዲዮ ፕሮግራሞች ጉዳዩን (ብሄራዊ መግባባትና እርቅን) የተመለከቱ ውይይቶች ተካሂደው ይሆናል:: ለዚህ ጥናት እነዚህን ሁሉ የመረጃ ምንጮች ማካተቱ ጊዜ ወሳጅ መሆኑ ታምኖበታል:: በመሆኑም ከላይ የተዘረዘሩትን የጥናቱን ዓላማዎች ለማሳካት በዋና ዋና ድረ ገጾች የታተሙ መጣጥፎችን መመልከት ጠቃሚና ጊዜ ቆጣቢ ሆኖ ተገኝቷል:: አንድም የተቀናጀ ጽሁፍ በድረ ገጾች ማውጣት የተለመደ ነውና:: በመሆኑም ይህ ጥናት አራት ዋና ዋና ድረ ገጾችን በመረጃ ምንጭነት ተጠቅሟል:: እነሱም ECADF Ethiomedia Ethiopian Review እና Zehabesha ናቸው:: እነዚህ ድረ ገጾች በኢትዮጵያዊያን ዘንድ በደንብ የሚታወቁና ፖለቲካዊ ማኅበራው ባህላዊ ሃይማኖታዊ ምጣኔ ሃብታዊና ሌሎችንም ጉዳዮች ያካተቱ በርካታና ጠቃሚ ጽሁፎች የሚታተሙባቸው ናቸው:: በአጠቃላይ ሲታይ እነዚህ ድረ ገጾች ስለብሄራዊ መግባባትና እርቅ በቂ መጣጥፎችን እንደሚያትሙ ይገመታል::  

በተመረጡት አራት ድረ ገጾችም የተጻፈውን ሁሉ አንድ በአንድ መፈተሽ አሰልቺና ጊዜ ወሳጅ ከመሆኑም በላይ አላስፈላጊም ነው:: በመሆኑም የእያንዳንዱን ድረ ገጽ የመፈለጊያ ሳጥን Search box በመጠቀም በጉዳዩ ላይ የተጻፉትን መጣጥፎች በቀላሉ ማግኘት ይቻላል:: ቀጥለው የተዘረዘሩትን የአማርኛና የእንግሊዝኛ የመፈለጊያ ቃላት ወይም ቁልፎች keywords በመጠቀም አራቱም ድረ ገጾች ተፈትሸዋል::
·         National dialogue
·         National consensus
·         National reconciliation
·         ብሄራዊ ውይይት
·         ብሄራዊ መግባባት
·         ብሄራዊ እርቅ

በሌሎች ድረ ገጾች ጉዳዩን በተመለተ መጣጥፎች ታትመው ስለሚሆን Google በመጠቀም ተጨማሪ ፍለጋ ተካሂዷል:: ይህንም ለማድረግ ከላይ የተዘረዘሩትን የአማርኛና የእንግሊዝኛ  የመፈለጊያ ቃላትን ተጠቅሜአለሁ:: በአጠቃላይ ሲታይ አራቱ ድረ ገጾች በርካታ በብሄራዊ መግባባትና እርቅ ላይ የተጻፉትን ይዘው ተገኝተዋል:: ዳሩ ግን በፍለጋው ያልተገኙ ጥቂት መጣጥፎች ሊኖሩ ይችሉ ይሆናል:: የጥናቱ ዋና ዓላማ ስንት እንደታተመ መቁጠር ሳይሆን ምን እንደተባለ መመርመር ስለሆነ ይህ ብዙም አያሳስብም:: ለአንባቢ ግልጽ መሆን ያለበት ሌላ ጉዳይ ቢኖር ይህ ጥናታዊ ጽሁፍ የሚያተኩረው የድኅረ 97 ምርጫ ጊዜን ነው:: ይህ ጥናት ምርጫውን ተከትሎ የነበሩትን የእርቅ ሙከራዎች አያጠቃልልም:: ምንም እንኳን ከዚህ ውጭ የጊዜ ገደብ ባይደረግም በርዕሱ ላይ የተጻፉት ጽሁፎች ለንባብ የበቁት ከ2010 ጀምሮ መሆኑን ግንዛቤ ወስጃለሁ:: የጥናቱ ዋና ዋና ግኝቶች ቀጥለው ቀርበዋል::      


የጥናቱ ግኝቶች

በአጠቃላይ ሲታይ ብሄራዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ 18 ጽሁፎች 2010 እስከ 2014 ታትመዋል:: ከዚህ ውስጥ ግማሽ ያህሉ 2014 ብቻ የታተሙ ናቸው:: አብዛኞቹ (14) 2013 እና 2014 የተጻፉ ናቸው:: ሰባቱ በአማርኛ ሲጻፉ ቀሪዎቹ 11 ደግሞ በእንግሊዝኛ ተጽፈዋል:: 16 መጣጥፎች አርእስትና ሙሉ ይዘታቸው ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ሲሆን ቀሪዎቹ ሁለቱ የተጻፉት ግን በሌላ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ነው:: ቢሆንም ግን ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ከተነሱት አበይት ጉዳዮች ውስጥ ይጠቀሳል:: አብዛኞቹ መጣጥፎችን ያቀረቡት ብዙውን ጊዜ በተለያዪ ሚዲያዎች የሚታወቁ ኢትዮጵያውያን ፕሮፈሰሮች ወይም ዶክተሮች ናቸው:: ሁሉም ጽሁፎች ከዚህ ጽሁፍ መጨረሻ ላይ በጸሃፍት ስም በታተሙበት ዓመት በርዕሳቸውና ጽሁፎች በታተሙባቸው ድረ ገጾች ተዘርዝረው ይገኛሉ አንባቢያን ጸሃፍትን በቀላሉ ይለዩአቸው ወይም ያውቋቸው ዘንድ ሙሉ ስማቸውን በቅንፍ ውስጥ ጠቅሻለሁ:: አንድ ጽሁፍ በተለያዩ  ድረ ገጾች ታትሞ ቢገኝም ይህ ጥናታዊ ጽሁፍ ግን መጀመሪያ የተገኘበትን ድረ ገጽ ብቻ ይጠቅሳል::


ምንም እንኳን ሁሉም ጽሁፎች ብሄራዊ ውይይት መግባባትና እርቅ ዋና ጉዳያቸው ቢሆንም በዝርዝር ያተኮሩባቸው ጉዳዮች እንዲሁም የሰጧቸው የመፍትሄ ሃሳቦች ግን የተለያዩ ናቸው:: በአጠቃላይ ሲታይ ግን የሚከተሉት ጉዳዮች በተለያዩ ጽሁፎች ተዳሰዋል:: 
·         የብሄራዊ እርቅ ጥቅምና አስፈላጊነት
·         እርቅ የሚያስፈልጋቸው አካላት
·         እርቁን ማን ማስተባበር ወይም መጀመር እንዳለበት
·         እርቁ እንዴት ሊካሄድ እንደሚችል 
·         ብሄራዊ እርቅና ፍትህ  እንዴት ሊታዩ እንደሚገባ


እነዚህን ጉዳዮች በተመለከተ የተገኙት 18 መጣጥፎች ምን እንዳስቀመጡ ቀጥሎ በአጭሩ ቀርቧል:: በቅንፍ የተመለከቱት የጸሃፍት ስምና መጣጥፎች የታተሙበት ዓመታት ናቸው:: ይህ ጽሁፍ የሚያተኩረው በዋናና ጠቅላላ ሃሳቦች ዙሪያ ስለሆነ ዝርዝር ጉዳዮችን ለመረዳት በአባሪ መልክ የተያያዙትን 18ቱን ጽሁፎች ማንበብ ይጠቅማል:: እንደገና የማሳስበው ጉዳይ ቢኖር 18ቱም ጽሁፎች ሁሉንም ከላይ የተዘረዘሩትን ንዑስ ጉዳች እንዳላተቱ ነው::    


የብሄራዊ እርቅ አስፈላጊነትና ጥቅም

ሁሉም ጽሁፎች ብሄራዊ መግባባትና እርቅ እጅግ ተፈላጊ የሆኑ ማኅበራዊ እሴቶችን ለመመስረትና ለማጽናት ወሳኝ እንደሆነ ያስገነዝባሉ:: እንዲሁም ከሌሎች የትግል ስልቶች አግባብነትና አተገባበር ጋር ብሄራዊ እርቅን ያወዳድራሉ ያነጻጽራሉ::  አብኞቹ ጽሁፎች ብሄራዊ እርቅ የሚያስፈልገው ኢትዮጵያ ያለችበት ዘርፈ ብዙ ችግር ተባብሶ ወደ ከባድ ቀውስ እንዳትገባ ስለሚያደርግ እንደሆነ ያትታሉ:: ያሉትን ችግሮች በህዝባዊ አመጽም ሆነ በጦርነት ለመፍታት አስቸጋሪ ከመሆኑም በላይ ተያይዞ ሊመጣ የሚችለው ቀውስ በቶሎ ማቆሚያ ሊኖረው እንደማይችል የብዙ አገሮችን ተሞክሮ በማንሳት ብዙዎች ያስጠነቅቃሉ:: ለምሳሌ ያህል ጥቂት ስለብሄራዊ እርቅ ጥቅም ወይም አስፈላጊነት የተሰጡት ማሳመኛዎች ቀጥለው ቀርበዋል::     
  • ውጥ በምርጫ ካልሆነ በጦርነት ካልተቻለ ህዝባዊ አመጽም አደጋ ካለው ብሄራዊ የእርቅ መንግስት ከመመስረት ውጭ ሌላ ምን አማራጭ የለም (መሳይ ከበደ 2013/2014)
  • የመንግስት ባለሥልጣናት ሳይቀሩ  ስለሚፈልጉ ብሄራዊ እርቅን ለመተግበር የማይቻል አይደለም (ጋ 2013)
  • በቋንቋ በዘር በሃይማኖት በፖለቲካ ምክንያት ጥላቻ ያደረባቸውን አካላት ለማገናኘት ይረዳል (ዊት ተሾመ 2013)
  • ብሄራዊ እርቅ በሚገባ ከተያዘና ከተጠናቀቀ አምባገነኖችን ሳይቀር ነጻ የሚያወጣ ነው ሁሉም ተሳታፊ ስለሚሆን ጦርና የጦር ወሬዎች ታሪክ እየሆኑ ይሄዳሉ ይህ መንገድ የሰው ህይወትም ሆነ ንብረትና ሃብት አያጠፋም በመሆኑም ይህ የፖለቲካ መስመር ጭስ አልባ ሊባል ይችላል ስለሆነም በሚያስፈራ ዝምታ ውስጥ ያለውን የሰፊውን የኢትዮጵያን ህዝብ ቀልብ ሊስብ ይችላል ለመግባባትና ለእርቅ የሚደረግ እንቅስቃሴ በዓለም ኅብረተሰብ ዘንድ ተቀባይነት ስላለው አስፈላጊውን ድጋፍና ማበረታቻ  ማግኘት  አይከብድም በመጨረሻም ይህ የትግል ስልት ቀጣይነት ያለው ሰላምና እድገት እንዲመጣ ፈር ይቀዳል (ክሉ አባተ 2013/2014)
  • ቀጣይነት ላለው ሰላምና ጤናማ ማኅበረሰብ ለመፍጠር መግባባትና እርቅ ማድረግ ወሳኝ ነው (ለአዲሲቱ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቂ አኢጋን 2014  


የሚታረቀው ማን ነው?

ይህን ጉዳይ በተመለከተ በቂ ትንተና አልተሰጠበትም:: ጠቅለል ያሉና ግልጽነት የጎደላቸው ሃሳቦች ግን ተቀምጠዋል:: ከአብዛኞቹ ጽሁፎች ጀርባ ተቀምጠው የሚገኙት ነጥቦች እንደሚያመላክቱት ከሆነ እርቅ የሚደረገው ወይም መደረግ ያለበት በመንግስትና በህዝቡ መካከል ነው:: መንግስት በዳይና ህዝብ ተበዳይ ስለሆኑ የሁለቱ መወያየት መግባባትና መታረቅ ወሳኝ እንደሆነ ያብራራሉ:: እንዲሁም አንዱ ህዝብ ወይም ብሄር ከሌላው ጋር በጥርጣሬና በመፈራራት ስለሚኖር መታረቅ እንዳለበትም የሚጠቁሙ አሉ:: በተጨማሪም መግባባትና እርቅ በግለሰቦች መካከል ያለውን ያልጠራ ስሜትም ለማከም ማገልገል እንዳለበት የጠቆሙ አሉ (አኢጋን 2014):: ከዚህ ባለፈ ግን ጉዳዩን ብትንትን አድርጎ ያስቀመጠ ጽሁፍ የለም:: 

አንዳንዶች (ለምሳሌ ያዕቆብ ኃይለማርያም 2014) ማን ከማን ተጣላና ነው እርቅ የሚያስፈልገው ብሎ መቀለድ ዋጋ እንፍል ሲያስጠነቅቁ ሌሎች (ለምሳሌ ቴዎድሮስ ኪሮስ 2014; ተክሉ አባተ 2014 )ደግሞ በደፈናው በእርቁ መሳተፍ ያለባቸው ተቃዋሚ ኃይሎችና ድምጹን ያጠፋው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ እንዲሁም የፖለቲካ እስረኞች መሆን እንዳለባቸው ይጠቁማሉ:: አኢጋን ደግሞ የመጀመሪያ ደረጃ እርቅ የሚያስፈልገው በዘር በቋንቋ በሃይማኖትና በፖለቲካ በሚለያዩ ቡድኖች መካከል ሲሆን ከዚያ ቀጥሎ ብሄራዊ እርቅ መደረግ እንዳለበት ይጠቁማል:: በአጠቃላይ ሲታይ እርቅ የሚያስፈልገው በህዝብና በመንግስት መካከል ብቻ ሳይሆን ወረድ ብሎም በየደረጃው መከናወን እንዳለበት ጽሁፎች ጠቁመዋል:: ይሁን እንጅ መንግስትና ህዝብ ዋናዎቹ እርቅ የሚያስፈልጋቸው አካላት እንደሆኑ ሁሉም ጽሁፎች ያመላክታሉ::      


እርቁን ማን ያስተባብረው? 

ብሄዊ እርቁን ማን ማስተባበር እንደሚገባው ግልጽ የሆኑ ሦስት ዋና ዋና አማራጮች ተቀምጠዋል:: አንድ እርቁን መጀመርና ማስተባበር ያለበት መንግስት እንደሆነ ያተቱ አሉ (ለምሳሌ ዘላለም  እሸቴ 2014; መሳይ ከበደ 2013/2014 እና ገላውዲዎስ አርአያ 2010):: ፍላጎትና ዝግጁነት ካለው መንግስት ካለበት ብሄራዊ ኃላፊነትና ካለው አቅም አኳያ ይህን የማስተባበር ሥራ ቢወስድ እንደማይከብደው ይገመታል:: ሁለት እርቁን መምራት ያለባቸው  ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ናቸው የሚሉም አሉ (ለምሳሌ ዋለልኝ መኮንን 2012 ቴዎድሮስ ስ 2014):: ይህ አማራጭ ከፖለቲካው ሜዳ በመንግስት እየተገፉ ያሉት ኃይሎች ሂደቱን እንዲመሩት ያመቻቻል:: ሦስት መንግስትና ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ዋና የእርቁ አካል ስለሆኑና በዳይና ተበዳይም ስለሆኑ ነጻና ገለልተኛ ኢትዮጵያውያንን ያቀፈ አስታራቂ ግብረ ኃይል የእርቁን ሂደት መምራት አለበት የሚሉም አሉ (ለምሳሌ ተክሉ አባተ 2013 2014)::

ከነዚህ አማራጮች ለየት ያሉም አሉ:: ሁሉን አቀፍ የምክክር ጉባዔ እንዲጠራ ያሳሰቡም አሉ (ሰሎሞን ታረከኝ 2011):: መገናኛ ብዙኅን አስተዋጽዖ ማድረግ እንደሚችሉ ቢጠቀስም ሂደቱን ማን እንደሚመራውና እንደሚጀምረው ግን ግልጽ አይደለም:: እንዲሁም ጣቱ ትውልድ ወደብሄራዊ እርቅ የሚያደርሰውን ውይይትና ምክክር በበላይነትና በባለቤትነት መምራት እንዳለበት ያሳሰቡ አሉ (አለማዬሁ ማርያም 2012):: የተማረጣቱ ትውልድ የትናንቱ ትውልድ ከሚዳክርበት የግራና የቀኝ የፖለቲካ አመለካከት ነጻ ሆኖ የእርቁን ሂደት ቢመራው እጅግ እንደሚሻል ተጠቁሟል:: ይህ እንዴት መካሄድ እንዳለበትም የመነሻ ሃሳቦች ተሰጥተዋል::    


እርቅ እንዴት ይካሄድ?

ብሄዊ መግባብትና እርቅ እንዴት መካሄድ እንዳለበት በርከት ያሉ ትንተናዎች ተሰጥተዋል:: ብዙዎች (ለምሳሌ ተክሉ አባተ 2014; ዘላለም እሸቴ 2014; ሰሎሞን ታረከኝ 2011; አለማዬሁ ገብረ ማርያም 2012; ላውዲዎስ አርአያ 2010)  ከእርቅ በፊት ቀጣይነት ያላቸውና ሁሉን አቀፍ ክርክሮችና ውይይቶች መካሄድ እንዳለባቸው ጠቁመዋል:: ብሄራዊ ክርክሮችና ውይይቶች መንግስትና ተቃዎሚ ድርጅቶች በእኩልነት ተናግዱ: የእያንዳንዳቸውን ጠንካራና ደካማ ጎን መለየት የሚያስችሉ: እንዲሁም በእውነት ላይ የተመረኮዙ መሆን እንዳለባቸው ተጠቁሟል:: ሌሎች ስለእርቅ ሂደት የተዘረዘሩ ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው::
  • በውይይቶች ጊዜ እውነታን መለየትና እውቅና መስጠት (ያዬ አበበ 2014)
  • ሊያጋጥሙ የሚችሉ ችግሮችን ቀድሞ መለየት: ከዚያም የስምምነት ሰነድ መፈራረም (ገለታው ዘለቀ 2014)
  • ችግሮችን መመርመር: ተጎጅዎችን መለየት (ዳዊት ተሾመ 2013)
  • የተሰሩ ወንጀሎችን መለየት: መከላከያና ደህንነት ተቋማት ገለልተኛ ድረግ: በነጻ የመናገር መብት ማስከ (ዋለልኝ መኮንን 2012)
  • መጀመሪያ ወጣቶች ኢ-መደበኛ ውይይቶችን በአካባቢያቸው መጀመር: ንቃተ ኅሊናን የሚያዳብሩ መርሃ ግብሮችን ማዘጋጀ: ውይይቶች ግልጽነትን ዲሞክራሲያዊ አሠራርን የተከተሉ: ሰብአዊ መብቶችንና ነጻነትን ማዕከል ያደረጉ ይሁኑ:: የራስን ችሎታና አቅም መመዘን: ያሉትን ተቋማት ለዚሁ ዓላማ መጠቀም: ከትናንቱ ትውልድ የአዙሪት ፖለቲካ መጠንቀቅና ከስህተቱ መማር (አለማዬሁ ገብረ ማርያም 2013)
  • መንግስት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለአገር እድገት አስተዋጽዖ እንደሚያደርጉ ይመን:: እነሱንም ከማሳደድና ከመፍራት ይልቅ ያቅርባቸው:: በዘር ላይ የተመሰረተውን የፌደራል አወቃቀር እንደገና ያጢነው (ገላውዲወስ አርአያ 2010)
  • የታሰሩትን ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ ፓርቲና የሃይማኖት መሪዎችና አባላትን በሙሉ መፍታት፤  የጸረ-ሽብርተኛ አዋጅ መሰረዝ፤ እና የፖለቲካ ፓርቲዎችና የሕዝባዊ ድርጅቶች አባላትና መሪዎችን በሽብርተኛነት የተፈረጁትንም አጠቃሎ የያዘ አንድ ጉባዔ በአዲስ አበባ ማካሄድ (ዕቆብ ኃይለ ማርያም 2014)
  • የብሄራዊ እርቅ መድረኮች ይዘጋጁ (ቴዎድሮስ ኪሮስ 2014)
  • ልብ የሆነ ይቅርታ መጠየቅና ማድረግ (ን 2014) 

እርቅና ፍትህ  

ብሄራዊ መግባባትና እርቅ በሚጀመርበት ጊዜ የፍትህ አገሯ ወዴት ይሆናል? ይህ ጥያቄ ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ አኳያ በቂ መልስ ያገኘ አይመስልም:: ከ18ቱ መጣጥፎች ውስጥ ሦስት የሚሆኑት ብቻ ይህን ጉዳይ በግልጽ አንስተዋል:: በጣም  ለተበደሉ ወገኖች ፍትህ (ለምሳሌ ካሳ) መደረግ እንዳለበት ጠቆም ያደረጉ አሉ (ያዬህ አበበ 2014; ን 2014):: በጣም የተበደሉት ወገኖች እነማን እንደሆኑና ምን አይነት ካሳ በማን መሰጠት እንዳለበት ግን የተብራራ ነገር የለም:: ከሁሉም ጽሁፎች ገለታው ዘለቀ (2014 ገጽ 4)የጻፉት የእርቅና የፍትህ ግንኙነት እጅግ በተሻለ መልኩ እንደሚከተለው ያብራራል:: ዋናው መልእክት እርቅ በሚደረግበት ጊዜ እንደአስፈላጊነቱ ፍትህም ሥራ ላይ ሊውልበት የሚችል እድል እንዳለ ያመላክታል:: የእርቅና የፍትህ ውሳኔዎች በአንድ ላይ ተጣጥመው መሄድ እንደሚችሉ ባህላችንን በምሳሌነት እያነሳ ይተነትናል::   

በስምምነት ላይ የተመሰረተ ባህላዊ ውህደት ብሄራዊ እርቅን በኢትዮጵያ የሚያየው እንደዚህ ነው። በዚህ ጽንሰ ሃሳብ መሰረት ብሄራዊ እርቁ ሪስቶሬቲቭ ጀስቲስን መሰረት ያደረገና በሚያድግ ዴሞክራሲ ችግሮችን ሊፈታ የሚችል ስምምነት ማለት ነው። ይህ ማለት ግን ሪትሪቢዩቲቭ ጀስቲስ ቦታ የለውም ማለት ኣይደለም። በኣሁኑ ሰዓት በከፍተኛ ሙስናና ከፍተኛ ወንጀል እየፈጸሙ ያሉ ሰዎች ይህንን ኣሳባችንን እያዩ እንደ ጅልነት ኣይተው ከስልጣን እስኪወርዱ በግፋቸው እንዲቀጥሉ በር ኣይከፍትም። የብሄራዊ እርቅ ሰነዱ እንደነዚህ ኣይነት ሰዎችን በቡድን እያየ ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ ወደ ፍርድ ሊያመጣቸው መቻሉ ኣያጠያይቅም። እንደ ቡድን እንደ ሃገር ኢኮኖሚያዊ ችግሮቻችንን ዝግ እያለ ሊሰራጭ በሚችል የሪዲስትሪቢዩሽን ዘዴ ተመጣጣኝ እድገት ለማምጣት መስማማት፣ ፖለቲካዊ ተሳትፎን ከባህላዊ ውህደት ስምምነት ኣንጻር ኣይቶ ከብሄር ፖለቲካ ኣውጥቶ በኣንድ ብሄራዊ ማንነት ስር ለመገንባት መስማማት፣ ዋና የሃገሪቱን ቋንቋዎችን ቁጥር መጨመር ኣጠቃላይ ፈውስን ለማምጣት ይጠቅማል። ኢትዮጵያ ሪስቶሬቲቭ ጀስቲስ ላይ እንድታተኩር የሚያደርጋት ለዘላቂ ሰላምና ልማት ኣንድነት የሚረዳት ሲሆን ይህ የፍትህ ኣሰጣጥ ዘዴ በኢትዮጵያ ቡድኖች ዘንድ የተባረከና የሚበረታታ ነው። የኦሮሞ ስርዓትን ብናይ ለሪስቶሬቲቭ ጀስቲስ ትልቅ ቦታ ኣለው። ይቅር ማለትን፣ በዳዩን ከመቅጣት ይልቅ ተበዳዩን መካስን ያበረታታል። ኣማራው ኣካባቢ ያለውን የሽምግልና ስርዓት ስናይ በኣብዛኛው ሪስቶሬቲቭ ጀስቲስ የሚበረታታበት ሁኔታ ኣለ። በደቡብ፣ በምስራቅ በተለይም በሶማሌ ክልል ይህ የፍትህ ስርዓት ከፍተኛ ተጽእኖ ኣለው ገለታው  


የማጠቃለያ ሃሳቦች

ይህ ጥናት ብሄራዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ በርካታ ጠቅለል ያሉ ጉዳዮችን ዳሷል:: ዝርዝር ትንተናዎችን ከዚህ በታች ከተዘረዘሩት መጣጥፎች ማግኘት ይቻላል:: ለማጠቃለል ያህል ግን ጥቂት ነጥቦችን ማንሳት ያስፈልጋል::

አንደኛ ምንም እንኳን የተዳሰሱት 18ቱ መጣጥፎች የብሄራዊ መግባባትና እርቅን ጠቀሜታና አስፈላጊነት ከሌሎች የትግል ስልቶች ጋር በማነጻጸርና በማወዳደር ለማቅረብ መሞከራቸው ክፉ ባይሆንም ጉዳዩን በሌላ መነጽር መመልከቱ ይበልጥ ጠቃሚ ነው:: ብሄራዊ መግባባትና እርቅ ተጀምሮ የተወሰነ አጓጊ ደረጃ እስኪደርስ ድረስ ሌሎችን ትግሎች ማቆም ላያስፈልግ ይችላል:: ሌሎች ትግሎች (ለምሳሌ የተቀናጀና ደረጃ በደረጃ የሚመራ ህዝባዊ እምቢተኝነት http://tekluabate.blogspot.no/2014/08/blog-post_6.html#more) ምናልባትም መንግስት የእርቁን ጉዳይ በሚገባ እንዲያጤነው ሊያስገድዱት ይችላሉ:: በመሆኑም የእርቅን ጠቀሜታ ለማውሳት ሌሎች ትግሎችን ማኮሰስ የግድ አይጠበቅም::

ሁለተኛ የተወሰኑ ጽሁፎች ህዝብ ለህዝብ መታረቅ እንዳለበት አሳስበዋል:: ምንም እንኳን ሃሳቡ በራሱ ክፉ ባይሆንም ለበርካታ ችግሮች ሁሉ ተጠያቂ የሆነውን አካል ማለትም መንግስትን ላላ አርገን እንድንይዝ የሚጋብዝ :: በመጀመሪያ ደረጃ ህዝብ ለህዝብ ሊጣላ አይችልም:: ከበስተጀርባ ያሉ ተንኳ የመንግስት ፖሊሲዎችና ፕሮፓጋንዳዎች የህዝብን ልብ ይከፍላሉ:: መንግስት ከትንኮሳው ሁሉ ታቅቦ ህዝቦች በሰላምና በአንድነት እንዲኖሩ ቢሰራ በአጭር ጊዜ ውስጥ የነበረን መከባበርና መተሳሰብ ይመለሳል:: ስለዚህ መታረቅ ያለበት መንግስ ከህዝብ ጋር ነው ብዬ አምናለሁ::

ሦስተኛ መንግስትም ሆነ ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች እውነተኛ እርቅን ጀምረው ማስተባበር ይችላሉ ማለት ዘበት ነው:: መንግስት እንደግለሰብ ቂመኛ በቀለኛና ትምክህተኛም ነው:: ለተቃዋሚዎች ያለው ንቀትና ጥርጣሬ መጠን የለውም:: እርቅን እሱ ቢጀምር የመሸነፍና የመዋረድ ያህል ይመለከተዋል:: ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ቢሆኑ ከመንግስት ጋር ያላቸው ቅራኔ እርቅ ለመጠየቅ የሚያበቃ አይመስልም:: ሰጥቶ የመቀበልና የማሳመን ችሎታና ፍላጎት እስካሁን አላየንም:: በመሆኑም ሌላ ገለልተኛና አንጻራዊ በሆነ መልኩ ንጹህ ኢትዮጵያውያን የተሰባሰቡበት አካል ያስፈልጋል:: ይህን አካል የሚያቋቁመው አካል: የሚቋቋምበት መስፈርት: የሚኖረው ዝርዝር የሥራ ድርሻ: የሚጠቀማቸው ዘዴዎች: ወዘተ ግን ጥርት ብለው ለውይይት ቢቀርቡ የተመረጠ ነው እላለሁ:: እንዲሁም ፍትህና እርቅ ምን ያህል የሚዛመዱና የሚቃረኑ እንደሆነ የኢትዮጵያን ተጨባጭ ሁኔታዎች ግምት ውስጥ በማስገባት አስቀድሞ መተንተን ያስፈልጋል::

በአጠቃላይ ይህ አስተባባሪ ኃይል ከእርቅ በፊት በእርቅ ጊዜና ከእርቅ በኋላ ሊሟሉ የሚገባቸውን ሁኔታዎች እጅግ በዝርዝር አዘጋጅቶ ለሚመለከታቸው አካላት ሁሉ አቅርቦና በውይይት አዳብሮ ሊንቀሳቀስ ይገባል:: ይህ ቀላል ሥራ ስላልሆነ የሚመረጡት ሰዎች ስሜታቸውን የሚቆጣጠሩና የሞራል ብስለት ያላቸው: አዋቂዎችና አስተዋዮች: እንዲሁም የመግባባትና ጫናን የመቋቋም አቅም ያላቸው ሊሆን ይገባል:: ልዩ ልዩ አይነት መስዋዕትም ለመክፈል የተዘጋጁ መሆን አለባቸው:: በመሆኑም ብሄራዊ መግባባትና እርቅ በብርቱ ልፋትና መከራ የሚመጣ እንጅ እንደሚታሰበው ሰላማዊ ብቻ ላይሆን ይችላል::    

የመጀመሪያው ችግር የሚሆነው ይህን አስታራቂ ኃይል ማቋቋም ነው:: ማን ነው ይህን ሊያነሳሳው የሚችለው? በተለያዩ  አካላትስ ተቀባይነት ይኖረዋል? ፍላጎትና ለኢትዮጵያ መልካም ራእይ ያለው ማንኛውም አካል ሊጀምረው ይችላል:: ቢያንስ ቢያንስ ይህ ጥናታዊ ጽሁፍ የገመገማቸውን 18ቱን በብሄራዊ መግባባትና እርቅ ላይ ያተኮሩ መጣጥፎችን ያቀረቡት ምሁራን በመመካከር ለጉዳዩ የሚሆን መሪ ሃሳብ roadmap ማዘጋጀትና ለውይይት ማቅረብ ይችላሉ:: ጥናቱን በማካሂድበት ጊዜ የታዘብኩትና ወደፊት ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ ግን አለ:: ሁሉም መጣጥፎች ራሳቸውን የቻሉና ሌላውን ለድጋፍም ይሁን ለትችት በፍጹም የማይጠቅሱ ናቸው:: ስለአንድ ጉዳይ በሚጽፉ ሰዎች መካከል ምንም አይነት መናበብ እንደሌለ አመላካች ነው:: ሁሉም የግል ሩጫውን ተያይዞታል:: ይህን አቁመን በአንድ ጉዳይ ላይ የምንጽፍ ሰዎች መናበብ ብንጀምርና የመነሻ ሃሳብ ብናቀርብ ብሄራዊ ግዴታችንን እንደመወጣት ይቆጠራል:: የያዘውን የወረወረ ፈሪ አይባልም!!!

ስለብሄራዊ እርቅ የተጻፉ ጽሁፎች

በአማርኛ የተጻፉ

በእንግሊዝኛ የተጻፉ


ነጻነት ለኢትዮጵያ!!!
ገንቢ አስተያየት ወይም ጥያቄ ካለዎት በteklu.abate@gmail.com ይላኩ!

Feb 5, 2014

የብሔራዊ እርቅ ጥያቄና ንቅናቄው በኢትዮጵያ - በሙሉአለም ገብረመድህን

ለብሔራዊ እርቅ ጥያቄ መታመን ወደ አተገባበሩ ይገፋል!
በዚህ አጀንዳ ለዓመታት ሲነሳና ሲወድቅ የነበረው የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ በገዥው-ግንባር በኩል አውንታዊ ምላሽ እንዲሰጠው የሚያስችል ንቅናቄ መፍጠር ስለሚቻልበት ሁኔታ ለውይይት መነሻ እንዲሆን በሚያስችል መልኩ ጥቂት ሐሳቦችን ለመሰንዘር እና የብሄራዊ እርቅ ጥያቄው በተደራጀ ህዝባዊ ንቅናቄ እንዴት መመራት እንዳለበት፣ እነማን ቢመሩት የተሻለ ይሆናል በሚሉ ጉዳዮች የሚለውን የግል ምልከታዬን ለመጠቆም እወዳለሁ፡፡ በዚህ ፅሁፍ የተካተቱ የንቅናቄው ሐሳቦችና ለብሄራዊ እርቅ ጥያቄው መታመን እስከቻልን ድረስ ወደ አተገባበሩ እንደሚመሩን ባለ ሙሉ ተስፋ ነኝ፡፡
ያልተመለሰው የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ!
የ1966ቱን አብዮት በመጥለፍ ወደ ስልጣን የመጣው ደርግ፤ መንበረ-ስልጣኑን ለማፅናት ሲል በሄደበት የአገዛዝ መንገድ እጅግ ቁጥራቸው የበዛ ውድ የአገሪቱን ልጆች ህይወት ቀጥፏል፡፡ ዛሬም ድረስ ቂሙ ያልሻረ የስነ-ልቦና ጠባሳ ጥሎ አልፏል፡፡  ደርግ መንግስታዊ ፍጅቱን እንዲያቆምና ብሄራዊ እርቅ እንዲያወርድ በጊዜው በነበሩ የፖለቲካ ኃይሎች ጥያቄ ቢቀርብለትም ‹‹እርቅ የሚባለውን የባልና ሚስት ጠብ አደረጋችሁት እንዴ?›› በማለት ከማገላበጥ በዘለለ አውንታዊ ምላሽ መስጠት ያልተቻለው የጁንታው ስርዓት የውድቀቱን ቀን በገዛ እጁ እዳፋጠነው የዘመነ-ደርግ ትርክት ያስረግጣል፡፡
ፍትሃዊ ማህበረሰብ እና ፖለቲካዊ ስርዓት ለመገንት የታገሉ ውድ የአገሪቱን ልጆች ቀጥፎ ካለፈው አገዛዝ በስም እንጂ በግብር የማይለየው ኢህአዴግ እየሄደበት ካለው የአገዛዝ መንፈስ የተነሳ ከመንግስታዊ ፍጅት እስከ ጅምላ እስር፣ ከብሄር ቅራኔ እስከ ጎሳ ግጭት፣ ከመንግስታዊ ሽፍትነት እስከ መንግስታዊ ሌብነት፣… ድረስ ያሉ ጥፋቶችን ያለ እርምት በተደጋጋሚ ያሳየ በመሆኑ ቁጥራቸው የበዛ አገር ወዳድ ምሁራን፣ ፖለቲከኞች፣ የሲቪክ ማህበራት መንግስት የብሄራዊ እርቅ ጥሪ እንዲያደርግ ደግመው ደጋግመው ቢጠይቁም አገዛዙ ጥልቅ ተሸናፊ ከሆነው ደርግ በተለየ መልኩ ለብሄራዊ እርቅ ጥያቄው በጎ ምላሽ መስጠት ተስኖታል፡፡ ባለፉት ሃያ ሶስት ዓመታት ውስጥ ቁጥር ስፍር የሌላቸው የእርቅና ሰላም እድሎች መክነዋል፣ ጥያቄው ሲቀርብለት ‹‹ማን ከማን የተጣላ ኖሮ ነው እርቅ የሚያስፈልገው›› የሚለው ምፀታዊ ንግግር ከገዥዎቻችን አንደበት ዛሬም ድረስ ይደመጣል፡፡ የትላንት ጥፋቶች ግን ዛሬም ድረስ ቅርፃቸውን አንጂ ይዘታቸውን ሳይቀይሩ እንደቀጠሉ ነው፡፡ የአገሪቱ የጥፋት አዙሪት ዛሬም ከሽክርክሪቱ ሊወጣ አልተቻለውም፡፡ ዛሬም እንደ ትላንቱ በደል የማንነት አካል ሆኗል፡፡ የፖለቲካ ትግልን በህገ መንግስታዊ ክበብ ስር ብቻ ለመተርጎም የመጫወቻ ሜዳው ጠቧል በሚል ነፍጥ ያነገቡ ኃይሎች ቁጥር አስራ አንድ ያህል እንደደረሱ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በህገ-መንግስቱ ጥላ ስር ያሉት ተቃዋሚ ፖርቲዎች አገዛዙ የመጣበትን የስልጣን መንገድ የመረጡ ኃይሎችን  ከማውገዝ ይልቅ ‹ለዚህ ውሳኔ የገፋቸው ራሱ ኢህአዴግ ነው› በሚል ጣታቸውን ገዥው ግንባር ላይ ከመቀሰር ወደኋላ ሲሉ አይታይም፡፡ ግንባሩ የሚያራምደውን የአገዛዝ መንፈስ ተከትሎ እስር፣ እንግልት፣ ስቅየትና ስደት በፖለቲካ ንፍቀ ክበብ ስር ያሉ ሰዎች የትግል መገለጫ ሆኗል፡፡ በገዥው ግንባር ስር ሁለት አስርታትን የተሻገረችው ኢትዮጵያ ዛሬም ድረስ የማህበረ-ፖለቲካና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዋ በቅጡ አልተፈታም፤ ይህን ተከትሎ በአገሪቱ የፖለቲካ አደባባይ ላይ ‹‹አብዮታዊ ሁኔታ››ዎች እየታዩ ነው፡፡ አገሪቱን ከደም-ባህር መታደግ ይቻል ዘንድ አንድ ብቸኛ አማራጭ አለ፤ ብሔራዊ እርቅና ሰላም፡፡
የብሔራዊ እርቅ ጥያቄ በተበጣጠሰ መልኩም ቢሆን ዛሬም ድረስ ተስፋ ባልቆረጡ ወገኖች በኩል ይቀርባል፡፡ በዛኛው ጫፍ ያለው አገዛዝ ግን የተለመደውን ምላሽ ከመመለስ አልቦዘነም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን፤ ኢህአዴግን ሊያስጨንቅ የሚችል የብሄራዊ እርቅ ጥያቄው በግዙፍ ህዝባዊ ንቅናቄ መታጀብ እስከ ቻለ ድረስ ግንባሩ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሃገር ላሉ የፖለቲካ ሃይሎች የብሔራዊ እርቅ ጥሪ ሊያደርግ ይችላል የሚል በጎ እምነት አለኝ፡፡ ቁም ነገሩ ለብሔራዊ እርቅ ጥያቄው መታመኑ ላይ ነው፡፡
ይህን ጥያቄ ወደ አደባባይ ገፍተው የሚያወጡ የንቅናቄው አራማጆችን እንደ አብነት በዚህ ፅሁፍ አካትቻቸዋለሁ፡፡ እነዚህን የንቅናቄውን አራማጅ ኃይሎች ለማነቃቃት፣ ሞራል ለመስጠት፣ በአቅም ግንባታ ስልጠና ለመደገፍ ምሁራን/ሙያዊ አበርክቷቸውን ያለስስት ሊሰጡ ይችላሉ ብዬ እንደ አርአያ-ሰብ ያጨኋቸው ብርቅዬ የኢትዮጵያ ልጆችን በአዲስ ንዑስ ርዕስ እንዲህ ገልጫቸዋለሁ፡፡
የንቅናቄው መጋቢዎች
ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም፣ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም፣ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ ፕ/ር ላጴሶ ጌልዴቦ፣ ፕ/ር ጌታቸው ሽፈራው፣ ዶ/ር እንድሪስ ሙሐሙድ፣ ልጅ ዳንኤል ጆቴ   (የኢት.አባት አርበኞች ማ/ር የወቅቱ ፕሬዘዳንት)፣ አቶ ቡልቻ ደምቅሳ፣ አምሳደር ዘውዴ ረታ፣ ወ/ሮ ማዕዛ አሸናፊ (የመጀመሪያዋ የኢትዮጵያ የህግ ባለሙያ ሴቶች ማህበር ፕሬዘዳንት የነበሩ)፣ ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን (የቀድሞው የንግድ ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ፕሬዘዳንት)፣ ጋዜጠኛ ማዕዛ ብሩ፣ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት፣ ኡስታዝ ሐሰን ታጁ፣ አርቲስት ሙሃሙድ አህመድ (በነገራችን ላይ እነኝህ ምሁራን እና ታዋቂ ግለሰቦች እንደማሳያ የተጠቀሱ ናቸው)
የሃገረ-ኢትዮጵያ የእውቀት አደባባይ በዝምታ እንደተዋጠ፣ እጅግ ብዙዎቹ ምሁራን ከህዝባዊ ተዋፅኦ እንዳፈገፈጉ፣ ጥቂት የማይባሉ ምሁራን ደግሞ ከስርዓቱ ጋር በጥቅመኝነት የተሳሰሩ እንደሆነ አይካድም፡፡ እነዚኞቹ ግን አንድም አካዳሚያዊ አቅማቸውና አገራዊ አበርክቷቸው ሁለትም ያላቸው ህዝባዊ ተቀባይነትና ተደማጭነት በሶስተኛ ደረጃ ደግሞ ምሁራኑ የሚወክሉት የህብረተሰብ ክፍል ያለ በመሆኑ የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ ንቅናቄውን በተደራጀና በተጠና መልኩ ለመጀመር እንዲያስችል ለንቅናቄው አራማጆች ተገቢውን ድጋፍ ቢሰጡ፣ ምሁራንን በመቀስቀስ የማነሳሳት ስራ ቢሰሩ፣ ባለ ሀብቶች ይህን የተቀደሰ አላማ በገንዘብ እንዲደግፉ ቢያበረታቱ፣ ህዝቡ የንቅናቄው ተሳታፊ እንዲሆን በየተሰማሩበት የሙያ ዘርፍ/ተቋም ቢቀሰቅሱ፣… የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ ንቅናቄውን ወደ አደባባይ ገፍቶ ለማውጣትና ገቢራዊ ለማድረግ ተኪ የሌለው አይነተኛ ሚና ይኖራቸዋል የሚለው እምነት የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ነው፡፡
እርግጥ ነው! የንቅናቄው መጋቢ ይሆናሉ በሚል ካጨኋቸው ምሁራን ውስጥ የተወሰኑት በአገዛዙ እስርና እንግልት የደረሰባቸው የተገፉ ሰዎች ቢሆኑም፤ ይህ ንቅናቄ በደልን በመርሳትና ይቅር በማለት መጀመር ያለበት በመሆኑ፣ ተበዳዮቹ የምህረት ፍቅራቸውን ለአገዛዙ በማሳየት ስራቸውን ቢጀምሩ ለትውልዱ ትልቅ ትምህርት ይሆናል፡፡
የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ ንቅናቄው አራማጆች
  1. የሲቪክ ማህበራት ሚና፡- በ2001 ዓ.ም የፀደቀውን የበጎ አድራት ማህበራት አዋጅ ተከትሎ የሲቪክ ማህበራት ቁጥር እንደተመናመነ በተለይም በአገር አቀፍ ጉዳዮች እና ፖለቲካ ነክ በሆኑ አጀንዳዎች ዙሪያ የሚሰሩ ማህበራት ጭራሹን እየጠፉ እንዳለ ይታወቃል፡፡ ይሁንና አገር ቤት ባሉ አገር ወዳድ ምሁራን፣ ባለ ሃብቶች፣ በጎ አድራጊ ግለሰቦች በኩል  የአቅም ግንባታ ስልጠና፣ የቁሳቁስና የገንዘብ ድጋፍ እስከተደረገላቸው ድረስ እንደ ሰ.መ.ጉ፣ የባለራዕይ  ወጣቶች ማህበር፣ የመግባባት አንድነትና ሰላም ማህበር ወ.ዘ.ተ የመሳሰሉት የሲቪክ ማህበራት ለዚህ አገራዊ ርዕይ ስኬት የመታመን እድላቸው ሰፊ ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡
እነኝህ ማህበራት፤ ምንም እንኳ ዛሬ ላይ በገንዘብ እጥረት የተነሳ በየ ክልል ከተሞች ቅ/ፅ/ቤቶችን በመክፈት ተደራሽነታቸውን ማስፋፋት እንዳልቻሉ ቢታወቅም፤ የንቅናቄው መጋቢ በሚል የተጠቀሱ ምሁራን ዘመኑን ሊያነፃ ለሚችለው ለዚህ ክቡድ ርዕይ ስኬት ሲባል ከማህበራቱ ጎን በመቆም ድጋፋቸውን የሚያሳዩ ከሆነ፤ እነኚህ ማህበራት እግረ ሙቅ የሆነባቸውን የበጎ አድራጎት ማህበራት አዋጅ ተቋቁመው ዛሬም ድረስ የማህበር ህልውናቸውን ማስቀጠል የቻሉ ናቸውና የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ ንቅናቄው ወደ አደባባይ እንዲወጣና ግቡ እንዲመታ የማድረግ እድል ይኖራቸዋል፡፡
ሲቪክ ማህበራቱ በንቅናቄው ጎዳና…
ከላይ ለማሳያነት የጠቀስኳቸው ሲቪክ ማህበራትና ሌሎችም በጋራ ትብብር የሚመሩት፤ ከማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ተፅዕኖ ነፃ የሆነ ‹‹የአገር ሽማግሌዎች የጋራ ምክር ቤት›› ማቋቋም የማህበራቱ ተቀዳሚ ተግባር ይሆናል፡፡
በዚህ የጋራ ምክር ቤት መቀመጫ ወንበር የሚኖራቸው አካላት ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል፣ የሙያ ማህራት፣ የእምነት ተቋማት፣… የሚወክል መሆን ይኖርበታል፡፡ (በነገራችን ላይ የም/ቤቱ አባላት ዋነኛ ተልዕኮ መንግስት የብሔራዊ እርቅ ጥሪ እንዲያደርግ ማሳመን፣ ሌሎች የፖለቲካ ኃይሎችና አገሪቱን ይወክላሉ የሚባሉ ሊሂቃን (Elites) የመንግስትን ጥሪ ተቀብለው የውይይቱ ተሳታፊ እንደሆኑ ቅድመ ሁኔታዎችን ማመቻቸት እንደመሆኑ መጠን የም/ቤቱ ወንበር የግድ የብሔር ተዋፅኦን መጠበቅ አይጠበቅበትም፡፡ ‹ኢትዮጵያ እንዴት ትበየን?› የሚለው ጉዳይ የእርቅና ሰላም ጉባኤው ተሳታፊ አካላት የሚወስኑት ይሆናል)
በእነ ፕ/ር ይስሃቅ የሚመራው ‹‹የአገር ሽማግሌ›› ቡድን በእውን ከመንግስት ያልተጣበቀ ስለመሆኑ የሚያሳይበት የቁርጥ ቀን/ጊዜ ይህ ይመስላል፡፡ በእርግጥም የአገር ሽማግሌው ቡድን በፖለቲካ ኃይሎች መሀከል ያሉ ቅራኔዎችንና ቁርሾዎችን ለማብረድ ብሎም እርቀ ሰላም ለማስፈን እየተጋ ያለ ከሆነ የድጋፍ ይሁንታውን በአዲስ መልክ ለሚቋቋመው የአገረ ሽማግሌዎች የጋራ ምክር ቤት በመስጠት አብሮ መስራት የሚችልበትን ሁኔታ የሚያመቻች ይሆናል፡፡
የጋራ ምክር ቤቱ መንግስትን ጨምሮ ከሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች (በሰላማዊም በትጥቅ ትግልም ከሚታገሉት፣ በአገር ውስጥም በውጭም ካሉት) ጋር የሚመክር ይሆናል፡፡ ም/ቤቱ ሌሎች የብሔራዊ እርቅ ንቅናቄው አራማጆች  የሚሰሯቸውን ስራዎች በተዋረድ የሚከታተል ቢሆን ይመረጣል፡፡ ሁሉም የንቅናቄው አራማጆች ዋነኛ አላማ በአገሪቱ ላይ ያንዣበበው ‹‹አቢዮታዊ ሁኔታ›› ወደ አልተጠበቀ ህዝባዊ አመፅ ከመቀየሩ  በፊት አገሪቱ በብሔራዊ  እርቅ እንድንነፃ ማድረግ እንደመሆኑ መጠን በዚህ ንቅናቄ ውስጥ ተዋረዳዊና የጎንዮሽ ግንኙነት ቢኖር ተናቦ ለመስራትም ሆነ ለሚፈለገው ግብ ተመራጭ አካሄድ ይመስለኛል፡፡

ሲቪክ ማህበራቱ የጋራ ምክር ቤቱን ትርጉም ባለው መልኩ ከማንቀሳቀስ አኳያ ቀዳሚ ኃይል የመሆናቸው ጉዳይ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ የብሄራዊ እርቅ ንቅናቄው አካቶነት ያለው እንዲሆን ከማስቻል አኳያ በክልል ከተሞች እየተዘዋወሩ ብሔራዊ እርቅን ባስመለከተ ህዝባዊ ስብሰባዎችን ማካሄድ፣ ሴሚናሮችን ማዘጋጀት፣ በብሄራዊ እርቁ ዙሪያ የሚያጠነጥኑ የጥናት ውጤቶች በምሁራን ተዘጋጅተው እንዲቀርቡ ህዝባዊ መድረኮችን ማመቻቸት፣ ለብሄራዊ እርቅ ንቅናቄው ድጋፍ የሚያደርጉ አጋር የሲቪክ ማህበራት (የውጭ አገራት) በኢትዮጵያ ባይኖሩም እንኳ በያሉበት ቦታ አለም አቀፉን ማህበረሰብ እንዲያነቃቁ ጥሪ ማስተላለፍ፣… በጥቅሉ  የብሄራዊ እርቅ ንቅናቄው ዋነኛ አራማጅ ሃይል የሲቪክ ማህበራቱ እንደ መሆናቸው መጠን፤ ለማንም የፖለቲካ ፓርቲ ባልወገነ መልኩ አገሪቱ ወደ ብሔራዊ እርቅና ሰላም የምታመራበትን ሁኔታ መፍጠር ተቀዳሚ ተግባራቸው ይሆናል፡፡
  1. የኃይማኖት ተቋማት ሚና፡- የብሄራዊ እርቅ ጥያቄውን ወደ አደባባይ ሊያወጡ ከሚችሉ የንቅናቄው አራማጅ ከሆኑ ተቋማት ውስጥ ዋነኞቹ የኃይማኖት ተቋማት ናቸው፡፡ ተቋማቱ በአገር ሽማግሌዎች  የጋራ ምክር ቤት ውስጥ ከሚኖራቸው አበርክቶ ባሻገር ‹‹በኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ›› ስም ለገዥው ግንባር ከፍተኛ አመራሮች በአገሪቱ ውስጥ እርቀ ሰላም እንዲወርድ ጥሪ ማስተላለፍ፣ ለእርቀ ሰላም ጥያቄው አውንታዊ ምላሽ እስከ ሚሰጥ ድረስ በቤተ ክርስቲያናት ‹ምህላ›፣ በመስጅዶች ደግሞ ‹ቁነት/ልዩ-ፀሎት› ማዘጋጀት፣ የክርስትና ዘማሪያን፣ የእስልምና መንዙማ ባዮች/ማዲህ/ እንደየ ኃይማኖታቸው እርቀ-ሰላም ላይ የሚያተኩሩ መንፈሳዊ ስራዎችን በተናጠልና በህብረ-ዝማሬ መልኩ በሲዲና በካሴት መስራት፣ በየ አምልኮ ቤቱ በኃይማኖት መምህራን/ኡስታዞች አማካኝነት እርቅና ሰላም፣ መግባባትና አብሮነት ላይ የሚያተኩሩ ምስባኮች ከመቸውም ጊዜ በተለየ ሁኔታ በየጉባኤው እንዲሰሙ፣ በየ እድር ጀመአውና ማህበራቱ ቅራኔ ውስጥ የገቡ የፖለቲካ ኃይሎች እርቀ ሰላም እንዲያወርዱ የሚጫኑ/የሚያስገድዱ አጀንዳዎችን መፍጠር፣… ወ.ዘ.ተ የመሳሰሉ እጅግ የተጠኑ ኃይማኖታዊ አበርክቶዎችን ምዕመናኑን ባሳተፈ መልኩ ማካሄድ የኃይማኖት ተቋማት ሚና ይሆናል፡፡ ይህን ለመሰለው ተግባር እንደ ማህበረ ቅዱሳን ያሉ በኃይማኖት ተቋማት ስር የተደራጁ ማህበራት ጉልህ ሚና ይኖራቸዋል ብዬ አምናለሁ፡፡
  2. የኪነ-ጥበብ ሙያተኞች ሚና፡- በረጅሙ የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ አገራዊ አጀንዳዎችን ወደ ህዝብ አይንና ጆሮ ለማድረስም ሆነ ለተከታዩ ትውልድ ከማስተላፍ አኳያ ኪነጥበብ አበርክቶዋ ላቅ ያለ እንደነበር ያስታውሷል፡፡ ለዚህ የቀደመ ተሞክሮ መታመን እስከተቻለ ድረስ፤ ሰዓሊያን፣ ቀራፂያን ደራሲያንና ድምፃዊያን የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ ንቅናቄውን በጥበብ  መንገድ በመግራት ወደ አደባባዩ የማውጣት  ጥበባዊ ኃይል ይኖራቸዋል፡፡ ሰዓሊያንና ቀራፂያን የእርቅ መንፈስን የሚያንፀባርቁ ስራዎቻቸውን በመስራት በኢግዚቢሽን መልክ ለህዝብ እይታ እንዲያበቁ ማድረግ፣ ደራሲያኑ በበኩላቸው ንቅናቄውን በሚደግፍ መልኩ ተከታታይ የወግና የግጥም ስራቻቸውን በልዩ ፕሮግራም ወደ ህዝብ የማድረስ ስራ መስራት፣ ድምፃዊያን ደግሞ በአገር ፍቅርና አንድነት፣ እንዲሁም በብሄራዊ እርቅና ሰላም ዙሪያ የሚያተኩሩ ዜማዎችን በተናጠል እና በህብረት በመሆን በተለያዩ ቋንቋዎች መስራት፣ በዚህ መንፈስ የተቃኙ የሙዚቃ ድግሶችን (ኮንሰርቶችን)  በአገር ቤትና በውጭ አራት ማዘጋጀት፣… ከኪነጥበብ ሙያተኞቻችንና የሙያ ማህበራቶቻቸው የሚጠበቁ ጥበባዊ ስራዎች ይሆናሉ፡፡
  3. የሚዲያ ተቋማት ሚና፡- አሁን ባለንበት ተጨባጭ ሁኔታ የደፋር ሃሳብ መንሸራሸሪያ የሆነው ብቸኛው መድረክ የግሉ የሚዲያ ዘርፍ ነው (የገዥው ፓርቲ የግራ ጥፍር የሆኑትን አያካትትም) የሚዲያ ተቋማት የአደባባይ ምክንያተኝነትና ህዝባዊ መነቃቃትን በመፍጠር ረገድ አይነተኛ ሚና አላቸው፡፡ በዚህ የንቅናቄ ክፍል፣፤ ሁለት ክንፎች ይኖራሉ፡፡ የመጀመሪያው ክንፍ የማህበራዊ ድህረ-ገጽ ሲሆን፤ በዚህ የንቅናቄ ክንፍ የብሄራዊ እርቅ ጥያቄውን ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ   ማስተዋወቅ በሚቻልበት መልኩ አልሞ መስራት ግድ ይላል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለየ መልኩ ከፍተኛ ተነባቢነት እያገኙ የመጡት የአገር ቤቶቹ ‹‹ድምፃችን ይሰማ!›› ኢቢቢ ኤን፣ ኢትዮ ቢባል የመሳሰሉት ‹‹ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ!›› የሚለውን ጥያቄ ከፍ በማድረግ የብሄራዊ እርቅ ጥያቄውን ማስተባጋት ተቀዳሚ ተግባራቸው ሊሆን ይገባል፡፡ ሁለተኛው የንቅናቄው ክንፍ ደግሞ የህትመት ሚዲያው ሲሆን፤ በብሔራዊ እርቅ አስፈላጊነት ዙሪያ የሚያተኩሩ ፅሁፎችን በርዕሰ አንቀፅ፣ በአብይ አጀንዳ፣ በልዩ ዳሰሳ፣ በሐተታዊ ትንታኔ፣… መልኩ ማዘጋጀት፣ ተከታታይ ልዩ እትሞችን ወደ አንባቢ ማድረስ፣ በብሄራዊ እርቅ ዙሪያ የሚያተኩሩ ቃለ መጠይቆችን ከምሁራን፣ ከፖለቲከኞች፣ ከሲቪክ ማህበራት፣… ጋር ማካሄድ እንዲሁም ‹ነፃ ሚዲያ የተረሱትን፣ የተገለገሉትን እና የተጨቆኑትን የማህረሰብ ክፍሎች ድምፅ ማሰማት እና ግፉአኑ በገዥዎቻችው ዝንጋታ የተነሳ ስለሚደርስባቸው በደል እየተከታተሉ ዘገባ መስራት ይጠበቅባቸዋል› ለሚለው የሙያው መርህ መታመን ንቅናቄውን ወደ አደባባይ ለማውጣት በአያሌው ይጠቅማል፡፡  


ተስፋ አለን!

የብሄራዊ እርቅ ጥያቄ በህዝባዊ ድጋፍ የታጀበ እንዲሆን ይቻል ዘንድ ንቅናቄው በተደራጀ መልኩ መካሄድ አለበት፡፡ የንቅናቄው መጋቢ ምሁራን እና ታዋቂ ግለሰቦች ሐሳቡን በቡድንም ሆነ በተናጠል እየመከሩበት ሲቪክ ማህራቱንና ሌሎች የንቅናቄው አራማጆችን ማሳተፍ በሚቻልበት ሁኔታ መጀመሪያ የግል አስተያየታቸውን በፅሁፍም ሆነ በቃለ-መጠይቅ መልኩ ለውይይት በሚያመች ሁኔታ ሃሳባቸውን ወደ ሚዲያው እንደሚያወጡት ተስፋ አለኝ፣ የንቅናቄው መጋቢ ምሁራን ሲቪክ ማህበራቱን በዕውቀታቸው እንደሚደግፉ፣ በየሚሰሩበት ተቋማት/ድርጅት አጀንዳውን በማንሳት የውይይት መንፈስ እንደሚፈጥሩ እምነቴ ነው፡፡ አሁን ያሉን የሲቪክ ማህበራት የአንድ እጅ ጣት የማይሞሉ ቢሆንም የንቅናቄው መጋቢ ምሁራን  ድጋፍ እስካልተለያቸው፣ ባለ ሃብቶች እጃቸውን እስከዘረጉላቸው ድረስ ጥያቄውን ወደ አደባባይ ገፍተው እንደሚያወጡት ተስፈኛ እንሁን፡፡ 

የኃይማኖት ተቋማት የገዥው ግንባር የፖለቲካ ክንፍ ሁነዋል የሚል የአደባባይ ሐሜት ቢኖርም ስለ ሰማያዊ ህይወታቸው የታመኑ፣ በኢትዮጵያዊነታቸው የማይደራደሩ የኃይማኖት መሪዎች እዳሉን አንርሳ፣ ተተኪ ወጣቶችም ለህዝብ አይንና ጆሮ ቅርብ እንደሆኑ አንዘንጋ፤ የጥቂቶች ጥረት፣ ብዙሀኑን ማነቃነቁ አይቀርምና ለብሔራዊ እርቅ ጥያቄው እንታመን!! የምሁራን ዝምታ ከእንቅልፍ በከበደ አርምሞ ቢመሰልም የገዛ ፍላጎታቸውን ያሸነፉ የአደባባይ ምሁራን ስላሉን በእርሱ እንበረታታ፤ የእርቀ ሰላም ማዕቀፍ በማዘጋጀትም ሆነ ንቅናቄውን በምሁራዊ ተዋስኦ በማጀብ እንዲተጉ አደራ እንበል፡፡… 

መንግስትንና  ህዝቡን ከማቀራረብ ባለስልጣናትን ለግል ጥቅማቸው የሚቀርቡ፣ የፖለቲካና የህሊና እስረኞችን ከመጠየቅ ልጃገረዶችን ደግሞ ደጋግሞ መጎብኘት የሚቀናቸው በእድሜ የገፉ ‹‹አርቲስቶች›› ያሉን በመሆኑ የምናፍርላቸውን ያህል፣ ህዝባዊ ተቀባይነት ያላቸው ጎምቱ አርቲስቶች መንፈሳቸው ከግፉአኑ ጋር ስለሆነ በንቅናቄው የፊት መስመር ተሰላፊዎቻችን ይሆናሉ፡፡ ሚዲያው ለዘመኑ ጣኦት በሰነዱ፣ በብሔር አጥር በታጠሩ፣ የመክሸፍ ጥልቅ ማሳያዎች በሆኑ ‹‹የሙታን ዲሞክራሲ›› አምላኪዎች እንደተወረረ ቀድመን የተረዳን ቢሆንም ለህዝብና ለሙያቸው የታመኑ፣ ከብሔር አጥር ተሻግረው ኢትዮጵያን ለዘላለም የሚያኖራትን መሰረት በሙያቸው መርህ ለመተርጎም የሚተጉ የሚዲያ ሰዎች አሉንና በእነርሱ ተስፋ አለን! 

ቀጣዩ ዘመን በአብርኆት ይገለጥ ዘንድ የብሔራዊ እርቅ ጥያቄ ንቅናቄው ክረምቱን በውይይትና በቀና የሀሳብ ሙግት እያብላላን በማቆየት መስከረምን ጠብቀን ወደ አደባባይ እንደምናወጣው ተስፋ አለኝ! ‹‹ተስፋ ማድረግ ሰው መሆን አይደል፡፡ ተስፋ አልቆርጥም›› (በአሉ ግርማ)

(የብሄራዊ እርቅ ጥያቄውን ወደ አተገባበር መግፋት በሚቻልበት ሁኔታ ተቃዋሚ ፓርዎች እና የዲያስፖራው ማ/ሰብ ሚና ምን መሆን አለበት የሚለውን ሃሳብ በተመለከተ ሳምንት እመለስበታለሁ)

Dec 22, 2013

Acknowledging Past Injustices: Mandela, Menelik and Bulcha - Yaye Abebe

We, Ethiopians, are greatly in need of Nelson Mandela’s wisdom. Our nation has predominantly young demographics: 65% of Ethiopians are under the age of 24 years old.1 The ‘65 percent’ generation needs to inherit a constructive political atmosphere and culture, and that is where Mandela’s future oriented wisdom can benefit us greatly.
Acknowledging Past Injustices: Mandela, Menelik and Bulcha

Nelson Mandela's strength and success may be attributed to the way he prioritized the challenges South Africans faced.  It is his focus on the future of all South Africans, black, brown and white, that brought forth the path of truth and reconciliation to South Africa. We can not forget past injustices, but we must acknowledge them to create a conducive political environment with the potential for building and modeling political consensus for the coming generation of Ethiopians, the 65 percent.

100th Anniversary

Two weeks ago Emperor Menelik's 100th death anniversary was observed by online medias and radio stations such as the Deutsche Welle Amharic service. Our past, like that of other nations, is controversial and contested, although, perhaps, what makes ours more painful and highly divisive is the denial, disregard and blatant condescending attitude demonstrated by those of us, who feel Emperor Menelik’s legacy is impeccable, towards Ethiopians who feel differently about Menelik.

Listening to the discussion2 on Deutsche Welle radio, I realized more the need for Ethiopians to learn from Mandela: Mandela did not ignore the concerns, fears and anger of  Afrikaners or white South Africans. Mandela would not have averted a civil war in South Africa had he only looked at the black and brown South African interest - that is the genius of Mandela.

Listening to the Deutsche Welle discussion, I was baffled by the two academicians who defended Menelik's legacy with religious fervor. Are some of us this much egotistical that we will not consider other Ethiopians' perspectives, like that of Bulcha Demeksa’s, without losing our composure and sanity? I think we can do better.

History as Absolute

History is neither closed nor absolute; there always is another side to historical claims and assertions documented by ruling elites. Every human history is a mixed bag, and this is due to the nature which we all humans share: we are imperfect and prone to err. Hence the attempt of white washing any historical figure is going against human nature and experience.

The underlying argument perpetuating the one sided historical claims of our historical figures may have to do with the belief that written historical account is complete and accurate, while all oral history is incomplete and unreliable.

This fallacious thinking and total reliance on written history alone creates a single sided, unbalanced, elite-favoring historical narrative. We need not forget that just because the ruling elite had access to written language does not mean what they documented is inerrant.

Instead of defending a one sided narrow, elitist and biased historical account, as the one and only authoritative account of a regime’s legacy, we need to question and broaden our assessment of historical events, processes and possibilities by also paying attention to oral narratives.

Reconciliation is Acknowledgment

The dismissiveness of previous regimes and their elites have directly and indirectly pushed our Eritrean brothers and sisters to their present predicament and suffering. It is time we Ethiopians learn from Mandela and not get blind sided by superiority complex and short sightedness that could possibly fragment and destroy our nation, but rather we need to listen to Ethiopians who look at Ethiopian history from different angles, with different emotions, feelings and assertions.

Reconciliation starts by acknowledging the other side's perceptions, emotions and feelings.

To Mr. Bulcha Demeksa and all other Ethiopians who feel differently about the legacy of the regime of Emperor Menelik II and other regimes in Ethiopia’s past, I have this to say:  I regret past injustices committed by the regimes of Emperor Menelik II and other rulers on Oromos and all exploited, oppressed and marginalized Ethiopians.

65Percent.org

The coming generation, the 65%, of Ethiopians needs to witness political reconciliation and consensus in Ethiopia for the purpose of breaking the cycle of political violence, and passing on a culture of constructive politics.  The young generation needs to learn better conflict resolution skills than resorting to Kalashnikovs and violent uprisings.

If you share my vision of advocating and initiating political reconciliation and consensus among Ethiopians, please visit us on  http://www.facebook.com/65percentorg - Facebook, https://plus.google.com/u/0/108436055155436125022/ - Goolge+ or www.65percent.org/forum  and let us began the discussion of developing the frame work for political reconciliation and consensus among Ethiopians.

1. CIA World Factbook, https://www.cia.gov/llibrary/publications/the-world-factbook/geos/et.html accessed on October 11, 2013

2. http://www.dw.de/p/1AUZS

Yaye Abebe is founder of 65Percent.org which advocates for political reconciliation and consensus among Ethiopians.

Dec 3, 2013

የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄና ፈተናዎቹ በኢትዮጵያ (ክፍል 2) – በዳዊት ተሾመ

4. የብሔራዊ ዕርቅ ፈተናዎችና የመፍትሄ አቅጣጫዎች


በኢትዮጵያ የብሔራዊ ዕርቅ ፈተናዎች የሚመነጩት ስለ ብሔራዊ ዕርቅ ባለን ግንዛቤና እኛ ከለንበት ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር ለመቃኘት በምናደረገው ጥረት ውስጥ ነው:: በኢትዮጵያ ውስጥ ስለ ብሔራዊ ዕርቅ ሲነሳ እንድ ዋነኛ መነጻጸሪያ ሁኖ የሚቀርበው በደቡብ አፍሪካ ውስጥ የተካሄደውን ብሔራዊ ዕርቅን ነው:: በአብዛኛው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሎች የሚታሰበው የደቡብ አፍሪካ ዕርቅ ምንም እንከን እንደሌለውና በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታም አንጻር ሊደገም እንደሚችል ነው:: ነገር ግን፣ የደቡብ አፍሪካ ብሔራዊ ዕርቅ ሂደት የራሱ የሆኑ ጉድለቶች ያሉበት ከመሆኑም በላይ ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ነባራዊ ሁኔታ አንጻርም ብዙ ልዩነቶች አሉት:: ስለዚህም፣ በኢትዮጵያ የሚያስፈልገው ብሔራዊ ዕርቅ ያለንበትን ነባራዊ ሁኔታ የሚመጥን መሆን አለበት:: ከዚህ አንጻር በኢትዮጵያ የብሔራዊ ዕርቅ ፈተናዎችንና የመፍትሄ አቅጣጫዎች እንደሚከተለው ቀርቧል::

ሀ) እውቅና ስለመስጠትና የብሔራዊ ዕርቁ አካሄድ ላይ ያሉ ፈተናዎችና የመፍትሄ ሃሳቦች ላለፉት ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነቶችና በደሎች እውቅና መስጠት ላይ የሚታዩት ችግሮች ሁለት አይነት ናቸው:: አንደኛው ችግር ያለፉትን በደሎች እውቅና መስጠት በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑ ነው:: ይኸ ማለት ላለፉት በደሎች እውቅና መስጠት ማለት በደሎችን የፈጸሙ ኃይሎች ለፈጸሙት በደሎች ተጠያቂነት ስለሚያመጠና በደሉን ፈጽመዋል የሚባሉት ደግም እንደ <ሀገር-መስራች፣ ስልጣኔ አስተዋዋቂና ሰለምና ብልጽግና አምጪ> በሚል በተለምዷዊው የኢትዮጵያ ታሪክ (meanistream Ethiopian history) ተክለ-ሰውነታቸው ስለተሳለ ነው:: ሁለተኛው ችግር ያለፉት በደሎች ዕውቅና ቢሰጥ ቀጥሎ ሊመጣ የሚችለው ነገር ላይ ብዥታ መኖሩ ነው:: ይህም ማለት ዕውቅና ቢሰጥ ተበድለናል የሚሉ የፖለቲካ ኃይሎች ለራሳቸው ፖለቲካዊ ጥቅም ሊያውሉት ይችላሉ የሚል ፍራቻ መኖሩ ነው:: እነዚህ ዕውቅና በመስጠት ላይ ያሉ ተግዳሮቶች በምንም መልኩ በደሎችን በመካድ ሊፈቱ አይችሉም:: እንደ አቅጣጫ መወሰድ ያለበት አካሄድ ያለፉትን በደሎች አለመካድና በድጋሚ እንዳይፈጸሙ ማድረግን ነው::

በሌላ በኩል ደግሞ፣ በደሎቹ የተፈጸሙበት ወቅት ያለውን የአስተሳሰብ ደረጃና የአገዛዛ ባህሪ ከጭፍን ስሜታዊነት ውጭ መመልከት ተገቢ ነው:: ታሪክ ለፖለቲካዊ ግብ መምቻ ብቻ ከመጠቀም ወጥተን ታሪክን ለታሪክ ተመራማሪዎች መተውን መልመድ መቻል አለብን:: በሀገራችን ሊኖረን የሚገባው ፖለቲካ ትላንትን መሰረት ያደረገ ሳይሆን በነገው ብሩህ ቀንና አብሮነታችን ላይ የተመሰረተ መሆን ይገባዋል:: ይህ ማለት፣ ሙሉ ለሙሉ ታሪክን ከፖለቲካ መነጥል ይቻላል ማለት አይደለም:: ይልቁኑም ፖለቲካችን በባለፈው ታሪካችንና በነገው አብሮነታችን እና ፍትሃዊ ተጠቃሚነታችን ላይ ያለውን ሚዛን ማስተካከል ቁልፍ መሳሪያ መሆን ይገባዋል::

በአገራችን የነበሩ አገዛዞች ምንም እንኳን ማህበረሰባዊ መሰረታቸውን በስነ-ልቦና ደረጃ ተጠቃሚ ያደረጉ ቢመስልም፣ በሁሉም በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ህዝቦች በባለፉት አገዛዞች ተበዳዮች ናቸው፤ የበደላቸው መጠንና የበደላቸው አይነት ምንም እንኳን ቢለያዩም:: ያለፉት አገዛዞችም ሆነ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ፓርቲ የጠቀሙት ጥቂት ከስርአቱ ጋር ቅርበት ያላቸው ልሂቃንን እንጂ በአጠቃላይ ልሂቃኑ የወጡበትን ወይም እንወክለዋለን የሚሉትን ማህበረሰብ አይደለም:: ስዚህም፣ ያለፉትን በደሎች ዕውቅና መስጠት ማለት ይህ ህዝብ በዚህ ህዝብ ተበድሏል፤ እከሌ የሚባል ህዝብ በዳይ እከሌ የሚባል ህዝብ ተጎጂ በሚል መንፈስ መሆን የለበትም:: ሁሉም ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነቶችም ሆነ በደሎች መታየት ያለባቸው በደሎቹን የፈጸሙት አገዛዞች ከተመሰረቱበት ፓለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረቶች የመነጩ መሆናቸውን ነው::

ይህ አካሄድ አንድ በኩል በህዝቦች መካከል ሊፈጠር የሚችለውን በቂም በቀል የታጀለ ማህበረሰባዊ ግንኙነት መሰረት እንዳይዝ ሲያረግ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ከባለፈው ታሪካችን ተምረን የተሻለ ነገን ለመፍጠር ለምናደርገው ሂደት ማህበረሰባዊ መነቃቃትን ይፈጥርልናል:: ስለዚህም፣ በዚህ አካሄድ ላለፉት በደሎች ዕውቅና በመስጠት ሊከሰት የሚችለው የፖለቲካ ኃይሎች ያለፉትን በደሎች ፖለቲካዊ ትርጉም በመስጠት ለፖለቲካ ጥቅም የሚያውሉበትን እድል ማጥበብ ይቻላል:: በመሆኑም፣ የብሄራዊ እርቅ ጉዳይ መታየት ያለበት የባለፈውን ጠበሳ በመነካከት ቅራኔን በማባባስ ፖለቲካዊ ትርፍ ለማስገኘት ሳይሆን ከባለፈው ታሪክ በመማርና ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነትን በማረም የተሻለ ነገንና ብሩህ-ተስፋን ከመፍጠር አንጻር መሆን ይገባዋል::

ለ) የተፈጸሙትን በደሎች ያስከተሉት ውጤቶች ላይ፣ ተጎጂዎች የከፈሉት መስዋትነት እና እንድምታ ላይ ስምምነት መድረስን (Consensus building) በተመለከተ ያሉ ችግሮችና የመፍትሄ አቅጣጫዎች በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር <ብሔራዊ ዕርቅ የሚያስፈልገው ለየትኛው ታሪካዊ በደል ነው> የሚለው ጥያቄ በተፈጸሙ በደሎች ላይ ስምምነት ለመድረስ ወሳኝ ጥያቄ ነው:: ኢትዮጵያ የአሁኗን ቅርጽ እንድትይዝ ካደረጋት የሀገር ግንባታ ሂደት አንስቶ አሁን እስከምንገኝበት ዘመን ውስጥ የተፈጠሩትን ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነትና በደሎችን ማካተት አለበት:: እነዚህን ሁሉ በደሎች አንድ ሰው ወይም አንድ አገዛዝ ሳይሆነ የፈጸመው፣ በየወቅቱ በሀገራችን የሰፈኑት አገዛዛችና አገዛዛቹን የመሰረቱት እና ተጠቃሚ በሆኑት ለአገዛዛቹ ቅርበት ባላቸው ጥቂት ልሂቃን ነው:: ስለዚህም፣ ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነት የጎደላቸው ነገሮች ተደግረዋል፤ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በአገዛዛቹ ተበድለዋል፤ የበደሉ አይነትና መጠን ቢለያይም:: ስለዚህም የተፈጸሙት በደሎች ያስከተሏቸው ውጤቶች በደንብ ተመርምረው ለታሪክ መማሪያነት መቀመጥ አለባቸው:: እንደ ሁሉም ሀገር፣ ሀገራችን ኢትዮጵያም ያላት ታሪክ <ጥሩም መጥፎ> ነው:: ከ<ጥሩ> ታሪካችን አንድነታችንን የበለጠ በማጠናከር <ከመጥፎው> ታሪካችን ደግሞ በመማር ማህበራዊ ግንኙነታችንን ይበልጥ በመተማመንና በመከባበር ላይ የተመሰረት ማድረግ እንችላለን:: ስለዚህም፣ የተፈጸሙት በደሎች ያስከተሉት ውጤቶችና ተጎጂዎች የከፈሉት መስዋትነትና እንድምታ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ ተመዝግቦ መያዝ ይገባዋል::

ለዚህም አላማ ሲባል ሊደረጉ የሚችሉ ተግባራት የሚከተሉት ሊሆኑ ይችላሉ:: አንደኛ፣ የኢትዮጵያን ታሪክ፣ በማህበረሰቡ ውስጥ የነበሩና ያሉ ግንኙነቶች፣ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በአግባቡ ሳይንሳዊ መሆነ መንገድ ተጠንተው እንዲቀመጡ በየዩኒቨርስቲዎቻችንና መንግስታዊ በሆኑ የምርምር ተቋማት ውስጥ እንደ አንድ ፕሮግራም ተቀርጾ ሊዘረጋ ይችላል:: በዚህም ሂደት የብሔራዊ ዕርቁን ተቋማዊ ገጽታ ማላበስ ይቻላል:: ሁለተኛ፣ ብሄራዊ ዕርቁን የሚመለከት መታሰቢያ ብሄራዊ ቀን ቢመረጥና በየዓመቱ የምርምር ስራዎች የሚቀርቡበት፣ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመፍጠር፣ በመከባበርና ፍትሃዊነት ላይ የተመሰረተ ግንኙነት በማህበረሰባችን ውስጥ ሊመጡ በሚችሉ ተግባራት ታስቢ እንዲውል ማድረግ ይቻላል:: ሶስተኛ፣ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ በታሪካዊ በደሎች ምክንያት ውድ ህይወታቸውን ላጡ፣ ከመኖሪያቸውና ከአካባቢያቸው ለተፈናቀሉ እና የተለያዩ መሰዋትነት የከፈሉትን ሰዎች ለማስታወስ ሃውልት እንዲቆም ማድረግ የሚቻል ነው::

ሐ) የተፈጸሙት በደሎች በድጋሚ እንዳይፈጸሙና የተገለሉ የማህበረሰብ ክፍሎች ፍላጎትና ደህንነት የሚያረግገጥ ስርአት ለመፍጠር መዋቅራዊ ለውጦችን ማምጣትና የፖለቲካ ውህደትን ማሳለጥን (Structural changes and institutionalization of the process of political integration)፣ ብሔራዊ ዕርቅ ማህበራዊ ለውጥን ለማማጣትና ዴሞክራሲያዊ ስርአት ለመገንባት እንደ ወሳኝ ግብአት የምንጠቀምበት ከሆነ፤ ብሔራዊ ዕርቅ ሂደት በራሱ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ነው:: ይህ ማለት የተፈጸሙት በደሎች በድጋሚ እንዳይፈጸሙና የተገለሉ የማህበረሰቦች ክፍሎች ፍላጎትና ደህንነት የሚያረጋግጥ ዴሞክራሲያዊ ስርአት መፈጠር አለበት:: ይህን ለማድረግም፣ የፖለቲካ ስርአቱ የሚመራበትን የጨዋታ ህግ ማውጣትና የጨዋታውን ህግ የሚመሩ ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን መገንባት ይጠይቃል:: ይህም ማለት በማህበረሰባችን ውስጥ መዋቅራዊ ለውጦችን ማምጣትን የሚጠይቅ ነው:: የሁሉንም የማህበረሰብ ክፍሎች ፍላጎቶችና ደህንነት ለማስከበር የፖለቲካዊ ስርአቱ ውስጥ ሁሉንም ተሳታፊ ማድረግ ግድ ነው::

ከዴሞክራሲያዊ ስርአት ውጪ በሀገራችን ያለውን ብዝሃነት ሊያስተናግድ የሚችል ስርአት የለም:: ዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ በመሰረቱ ሁለት ግቦች ላይ ማነጣጠር አለበት:: አንደኛ፣ በዴሞክራሲያዊ ተቋማት ግንባታ ሂደት ውስጥ ተቋማት የሚወክሉት ግለሰቦችን አሊያም የተወሰኑ የልሂቃን ቡድኖችን አይሆንም:: ተቋማት የሚወክሉት ስምምነት የተደረሰባቸውን የጨዋታ ህጎችን ሲሆን እነዚህም ህጎች በልሂቃን ውስጥ የሚፈጠሩ የጥቅምና የፍላጎት ግጭቶችን ለመዳኘት ዋና መሳሪያ ይሆናሉ:: ስለዚህም፣ የብሔራዊ ዕርቅ ሂደት ዴሞክራሲያዊ ተቋማትንና የጨዋታ ህጎችንና ደንቦችን ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች በሚስማሙበት መልኩ ለመቅረጽ የሚያስችል ሂደትን ይፈጥራል:: ይኸም ማለት ብሄራዊ ዕርቅ ከሚመጣባቸው ዋነኛ ሂደቶች መካከል የጨዋታ ህጎቹ የሚወጡበት አግባብና ሂደት ወሳኝ ነው:: ኢህአዴግ ብሔራዊ ዕርቅን የሚመለከትበት አግባብ ማለትም << ብሔራዊ ዕርቅ ማለት አሁን በለው ህገመንግስና ህገመንግስታዊ ስርአቱ ላይ መግባባት መፍጠር ነው::>> የራሱን ፖለቲካዊ የበላይነት ለማስጠበቅ ያለፈ ትርጉም አይኖረውም:: ምክንያትቱም የጨዋታ ህጎቹ የወጡበት አግባብና ሂደት ሌሎች የፖለቲካ ኃይሎችን ያገለለ ከመሆኑም በላይ ዋነኛ ተገዳዳሪ የሚባሉትን በተለይ ደግሞ ሀገር-አቀፍ ፖለቲካ የሚያራምዱትን ያላካተተ ነው::

ሁለተኛ ደግሞ በዴሞክራሲያዊ ስርአት የስልጣን ክፍፍልን ስለሚያመጣ፣ ተጠያቂነትን ስለሚያሰፍንና ፖለቲካዊ ስልጣን በጉልበት ሳይሆን በህዝብ ፍላጎት ላይ በተመሰረተ አካሄድ ስለሚያዝ አዲስ ፖለቲካዊ ባህልን በሃገራችን ውስጥ እንዲሰፍን ያደርጋል:: ስለዚህም፣ ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ የስልጣን ክፍፍሎሽ ስለሚኖር በልሂቃኖች መካከል ሊኖር የሚችለው የስትራተጂና የታክቲክ ጉዳይ እንጂ ጫፍ የወጣ ፖለቲካዊ ልዩነት አይሆንም:: በመሆኑም የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄ መዋቅራዊ ለውጥ ከማምጣትና ፖለቲካዊ ውህደትን ከማሳለጥ አንጻር መታየት ያለበት ነው:: ይኸም፣ ፖለቲካዊ ውህደት የጋራ ነገን ከመፍጠርና የጋራ ራዕይ እንዲኖረን እና አዲስ ሲቪክ ፖለቲካዊ ባህል እንዲገነባ ከማስቻሉም በላይ ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ መሰረት ይሆናል::

መ) ፈጣን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት በማምጣት ኢኮኖሚያዊ ውህደትን ማረጋገጥ (enhancing socio-economic development and economic integration)

በታሪካችን እንደምንመለከተው ከሆነ በአብዛኛው በልሂቆቻችን መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶች በፖለቲካ ሃሳቦች ልዩነት ላይ የተመሰረቱ ሳይሆን አንዱ አንዱን ጥሎ በማለፍ የፖለቲካ ስልጣን ለመቆጣጠር በሚደረጉ ግብግቦች ላይ የተመሰረቱ ናቸው:: የፖለቲካ ስልጣን ጥያቄ በዋናነት የሚያያዘው ደግሞ የሀገሪቱን ሀብት ከመቆጣጠር ጋር ነው:: በግልጽ ለማስቀመጥ ያክል የዘመናዊት ኢትዮጵያ ሀገር ምስረታ ሂደት ፖለቲካዊው እንድምታው ያልተማከለና በጣም ጠንካራ ማዕከላዊ መንግስት መመስረት ሲሆን፣ ኢኮኖሚያዊው እንድምታው ደግሞ በጦር አሸናፊ ሆነው የማዕከላዊ  መንግስት ምስረታን ሂደት የተቆጣጠሩትን ኃይሎች የኢኮኖሚ ጥቅሞችን የማስከበር ሂደት ነበር:: ይህ ሂደት በደርግ አገዛዛም ሆነ በኢህአዴግ አገዛዝ የተደገመ ነው:: በዘውዳዊው፣ በደርግም ሆነ በኢህአዴግ አገዛዞች የተዘረጉት ኢኮኖሚያዊ ስርአቶች የሰፊውን ህዝብ ተጠቃሚነት ያላረጋገጡና የአገዛዞቹን ቀጣይነት ብቻ ለማረጋገጥ ያለሙ ናቸው:: ይህም በመሆኑ የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄ ኢኮኖሚያዊ ፍትሃዊነትንና የህዝብ ተጠቄሚነት ላይ ያነጣጠረ መሆን ይገባዋል::

እንደ ደቡብ አፍሪካ ፖለቲካዊ ስልጣን ላይ ብቻ የተመሰረት የብሄራዊ ዕርቅ ሂደት በኢትዮጵያ ውስጥ ረጅም ርቀት የማይወስድ ብቻ ሳይሆን ወደ በለጠ ማህበረሰባዊና ፖለቲካዊ ችግሮች የሚያጋልጥ ነው:: ስለዚህም የኢኮኖሚዊ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ አንዱ የብሔራዊ ዕርቅ ዋና አላማ መሆን ይገባዋል:: በሌላ በኩል ደግሞ፣ የኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ፈጣን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን ማረጋገጥ እና በክልሎች መካከል ኢኮኖሚያዊ ግንኙነቶችን ማጠናከር እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው:: ድህነት በራሱ ሰዎች በወደፊት ሕይወታቸው ላይ ተስፋ እንዲቆርጡ፣ ጨለምተኛ እንዲሆኑ ከማድረጉም በላይ ለዚህ ሁሉ ቀውስ ተጠያቂ የሚያረጉት አንድ ነገር ይፈልጋሉ፤እራስን ከጥፋተኝነት ነጻ ለማውጣት:: ስለዚህም ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነቶችን ለዛሬው ውድቀት ብቸኛ ተጠያቂ እንደሆኑ ሲታሰብ፣ በተወሰኑ ልሂቃን ደግም ይህን ስሜት ለራሳቸው ፖለቲካዊ ጥቅም እንዲውል ያደርጋሉ፣ እያደረጉም ነው:: ስለዚህም፣ ፈጣን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን ማስፋን የብሔራዊ ዕርቅ ውጤታማነትንና ዘላቂነትን ከማረጋገጥ አንጻር ወሳኝ ነው::

ከዚህ ጎን ለጎን፣ ሙስናን ማስወገድ የሚያስችሉ ተቋማዊ፣ ህጋዊ እና አስተዳደራዊ ሪፎርሞችን ማካሄድ ግድ የሚል ነው:: በአሁኑ ሰአት የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ በቁጥጥር ስር ያዋሉት ሶስት ኢኮኖሚያዊ ሃይላት ናቸው:: እነርሱም፣ መንግስት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚቆጣጠራቸው ድርጅቶች፣ የሚድሮክ ድርጅቶች እና በኢፈርት ድርጅቶች ናቸው:: ይህም፣ የአሁን ኢኮኖሚ ስርአት በዋናነት የፖለቲካ ስልጣን የተቆጣጠሩት ጥቂት ልሂቃን የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በቀጥታ የሚቆጣጠሩበትን አግባብ ተቋማዊ ገጽታ የሚያላብስ ነው:: ስለዚህም፣ ፈጣን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትና ከዚህ ልማት እኩል ተጠቃሚነትን ከማስፈን አንጻር ሙስናን ማስወገድና ተወዳዳሪነትን የተላበሰ ኢኮኖሚያዊ ስርአት መዘርጋትን ግድ የሚል ነው:: በሌላም በኩል፣ በባለፉት የአገዛዝ ስርአቶች ከኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልማት ትሩፋት የተገለሉ የማህበረሰብ ክፍሎች ይበልጥ ተጠቃሚ ማድረግ ይገባል:: ይኸም፣ በባለፉት አገዛዞች ተበድለናል የሚሉ የፖለቲካ ልሂቃን ጫፍ የወጣ የፖለቲካ አቋማቸውን እንዲያስተካክሉ የሚስገድዳቸው፣ የማያስተካክሉ ከሆነ የማህበረሰባዊ መሰረታቸው እንዲያጡ የሚያደርግ፣ ከተናጥል ጉዞ የአብሮነት ጉዞ እንደሚበልጥ ሰፊው ህዝብ እንዲረዳ የሚደርግ ነው:: በመሆኑም፣ ይህ ሁኔታ የብሄራዊ ዕርቅ ዘላቂነትን ከማረጋገጡም በላይ ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ ወሳኝ ነው::

ሠ) ለብሔራዊ ዕርቅ ምቹ ሁኔታን ስለመፍጠርና አማራጭ መፍትሄዎች

እስካሁን ድረስ ብሔራዊ ዕርቅን ለማሳካት ምቹ ሁኔታን አልተፈጠረም:: ይህ ምቹ ሁኔታ አለመኖር የሚመነጨው ከገዢው ፓርቲ ከፋፍሎ የመገዛዝ ባህል እና በተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጣዊ ደካማነትና የጋራ አላማ መፍጠር አለመቻላቸው ነው:: ብሔራዊ ዕርቅ እንዲሳካ ስልጣን ላይ ያሉ ገዢዎችን የሚያስገድድና የሚገዳደር ተቃዋሚ ኃይል መኖርን ግድ የሚል ነው:: ካለ ጠንካራ ተቃዋሚ ኃይል የሚገኝ ብሔራዊ ዕርቅ፣ ዕርቅ ሊባል የሚቻል አይደለም:: ምክንያቱም የዕርቅ ሂደቱ ስልጣን ላይ ያሉ ልሂቃንን ጥቅም የሚያስጠብቅ ነው፤ ሁሉን የፖለቲካና ማህበረሰባዊ ኃይላትን የሚያካትት አይደለም:: ከዚህ ቀደም በወጡ ጹሁፎቼ እንዳመለከትኩት፣ የኢትዮጵያ የተቃውሞ ኃይሎች በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ ሀገር ያሉት በብዙ ችግሮች የተተበተቡ ናቸው:: የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄ ግማሹ ምላሽ በተቃውሞ ኃይላት ጥንካሬ ላይ የሚመሰረት ነው:: አንድነት ጥንካሬ፣ መከፋፈል ድክመትን እንደሚያመጣ ከባለፈው ታሪካችን በተሻለ ሁኔታ ልንማርበት የምንችልበት መድረክ የለም:: ስለዚህም፣ በተቋማዊ ብቃት፣ በስትራተጂ፣ በታክቲክ እና አባላትን በማፍራት ተቃዋሚ ሃይላት ከገዢው ፓርቲ ጋር ተገዳዳሪ መሆን አለባቸው::

አብዛኞቹ የሀገራችን የተቃውሞ ፖለቲካ ፓርቲዎች ልዩነታቸው ርዕዮተ አለማዊ፣ ስትራተጂያዊ ወይም ፖሊሲ ላይ የተመሰረተ ሳይሆን በግለሰቦች ቁርሾ ላይ የተመሰረተ ነው:: ስለዚህም፣ ግለሰባዊ ቁርሾዎችን ከብሔራዊ ፖለቲካ ጥያቄ መለየት መቻል አለብን:: በሌላም በኩል፣ አሁን የሚታየው የፖለቲካ ኃይሎች መሰባሰብ ይበል የሚያስብል ሲሆን፣ እዚያው ሳለም ሁሉን ማህበረሰብ የሚያቅፍና የሚያንቀሳቅስ አጀንዳ መቅረጽ ይጠበቅባቸዋል:: ተቃዋሚ ኃይላት ማህበረሰባዊ መሰረታቸውን መስፋትና ሁሉን የማህበረሰብ ክፍል (cross-cutting social cleavages) ማቀፍና ማንቀሳቀስ መቻል አለባቸው:: ይህን በማድረጋቸው፣ ገዢው ፓርቲ ስልጣን ላይ ብቻውን ለመቀመጥ የሚከፍለው መሰዋትነት በዕርቅ ሂደት ውስጥ በመሳተፍና ፖለቲካዊ ስርአት ለውጥ በመምጣቱ ከሚያጣው ጥቅም ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ እንዲሆን ያደርገዋል:: ይኸም፣ ለዘብተኛ የአገዛዙን ልሂቃን ወደ ብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄን እንዲያራምዱ ሲያስችላቸው፣ አክራሪ ልሂቃንን ደግሞ የበለጠ ደካማ ያረጋቸዋል::

በሌላ በኩል ደግሞ፣ የብሔራዊ ዕርቅ ስትራተጂያዊ ውጤቶችና ዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባት ሂደት ተጠቃሚዎች ጥቂት ልሂቃን መሆን የለባቸውም:: በብሔራዊ ዕርቁ ሂደት ማንም የፖለቲካ ኃይል ሳይሆን አሸናፊ የሚሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ ፍላጎት፣ አንድነት እና ሉአላዊነት ነው:: ስለሆነም፣ የብሔራዊ ዕርቅ ሂደት ማነጣጠር ያለበት ማን ስልጣን ላይ ወጣ የሚለው ሳይሆን ዴሞክራሲያዊ የጨዋታ ህጎች ማውጣት እና ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን መገንባት ላይ ነው:: ይኸም፣ የብሄራዊ ዕርቁ ስተራተጂያዊ ውጤቶች (ዴሞክራሲያዊ ስርአት፣ ፍትሃዊ ተጠቃሚነትና ሀገራዊ መግባባት) እና ታክቲካዊ ግቦች መካከል አንድነትንና ሚዛንን የሚያስጠብቅ ይሆናል:: በመሆኑም፣ እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ነጥቦች ለብሔራዊ ዕርቅ ምቹ ሁኔታን ከመፍጠሩም በላይ ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ ወሳኝ ግብአት ነው::

5. ማጠቃለያ

ሀገራችን ኢትዮጵያ በብዙ ውስብስብ ታሪካዊ ሂደት ያለፈች ሀገር እንደመሆኗ መጠን፣ ያሉብን ችግሮች መጠነ ሰፊና ውስብስብ ናቸው:: እስካሁን ድርስ ጉልበት ላይ የተመሰረተ ልዩነቶችን የመፍታት ሂደቶች የበለጥ ልዩነቶችን ውስብስብ እንዲያደርግና ጥላቻ ላይ የተመሰረተ ፖለቲካ ስር እንዲሰድ ሆኗል:: ምንም እንኳን ከደርግ ወታደራዊ አገዛዝ ውድቀት በኋላ የተለያዩ የብሔራዊ ዕርቅ አስተሳሰቦች በሙሁሯንና በፖለቲካ ኃይላት ቢራመዱም፣ የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄን የፖለቲካ ኃይላት የፖለቲካ ፍላጎታቸውን ማሳኪያ መሳሪያ ያደረጉበት አረዳድ እንደሰፈነ መረዳት አያዳግትም:: የብሔራዊ ዕርቅ ሂደት ውስብስብ ችግሮችን የምንፈታበት ሂደት እንደመሆኑ መጠን በእንዳንዱ ጥቃቅን በደሎች ላይ የምናተኩርበት፣ ፖለቲካዊ ትርፍ የምናሰላበት፣ አግላይ ስርአት የሚመሰረትበት ሂደት ሳይሆን የተሻለች ኢትዮጵያንና ብሩህ ቀን የመፍጠር ሂደት አካል መሆን ይገባዋል::

በዳዊት ተሾመ (dawit-teshome@hotmail.com)

ምንጭ፦ http://www.zehabesha.com/amharic/archives/10340

Nov 24, 2013

የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄና ፈተናዎቹ በኢትዮጵያ (ክፍል 1) - በዳዊት ተሾመ

ከደርግ የ17 አመታት የአገዛዝ ውደቀት በኋላ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሎች በስፋት ሲንጸባረቁ ከነበሩ ጥያቄዎች መካከል የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄ ዋነኛው ነው::


በዚህ ወቅት ውስጥ ለብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄ በፖለቲካ ኃይሎች የቀረቡት የመፍትሔ ሃሳቦች የተለያዩ ቢሆንም የመፍትሔ ሃሳቦቹ የሚመነጩት ግን በዋናነት ከሁለት ተገዳዳሪ አስተሳሰቦች ነው:: አንደኛው አስተሳሰብ የሚያጠነጥነው የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄው የሚካትተው ከኢትዮጵያ ዘመናዊ የሃገር ግንባታ ጋር ተያይዞ የተፈፀሙ ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነትንና በደሎችን እንዲሁም በያ ትውልድ ውስጥ የተፈፀሙ መጠፋፋትን አካቶ ሁሉን-አካታች መድረክ በማዘጋጀት ያለፈውን በደሎች ዕውቅና በመስጠት በፖለቲካ ሊህቃን መካከል መግባባትን ማስፈንን ነው:: ሁለተኛው አስተሳሰብ የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄን የሚመለከተው ኢትዮጵያን እንደ ሀገር በአዲስ መሰረት ላይ የመገንባት ሂደት አድርጎ ነው:: ይህም ማለት የብሔራዊ ዕርቅ ጥያቄ የሚያቅፈው ሁሉንም አይነት ማለትም ብሔር፣ ሃይማኖት እንዲሁም መደብ ላይ መሰረት ያደረገ ኢ-ፍትሃዊነትና መገለልን ከኢትዮጵያ ዘመናዊ የሃገር ግንባታ ጀምሮ የኢህአዴግን የአገዛዝንም የሚያካትት ነው። ተጨማሪ ያንብቡ




Nov 4, 2013

በህወሃት ውስጥ የዕርቅ ሃሳብ መነሳቱ ተሰማ - ጎልጉል

በህወሃት ውስጥ የዕርቅ ሃሳብ መነሳቱ ተሰማ


"የኢህአዴግ የአፈና ገመድ ነትቧል፣ ድርጅቱ ተናግቷል"

ኢትዮጵያ ግራ በሚያጋባና ሊተነበይ በማይችል የፖለቲካ ቀውስ ውስጥ መገኘቷን ያመኑ የህወሃት ሰዎች መካካል የእርቅ ሃሳብ ላይ ለማተኮር እቅድ እንዲያዝ ሃሳብ ማንሳታቸው ተሰማ። ኢህአዴግ የቀድሞው የአፈና ገመዱ መንተቡን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየታቸውና አለመተማመን መንገሱ ተጠቆመ።

ጎልጉል መረጃ በመስጠት የሚታወቁ የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራርና ዲፕሎማት እንዳሉት ህወሃት ውስጥ “እርቅ አስፈላጊ ነው” በሚል እቅድ እንዲያዝና እንዲሰራበት ሃሳብ ቀርቧል። በድርጅቱ ውስጥ በተፈጠረ አለመተማመን ሳቢያ ስጋት የገባቸው የህወሃት ሰዎች የእርቅ ሃሳብ እንዲሰራበት ያቀረቡት ሃሳብ ግን በመደበኛ ስብሰባ አይደለም። ተጨማሪ ያንብቡ


ምንጭ፦ http://www.goolgule.com/tplf-in-search-of-reconciliation/

ተልዕኳችን | Our Mission

“65 ፐርሰንት” ትርጉም? የኢትዮጵያ ህዝብ 65 በመቶው እድሜያቸው ከ24 አመት በታች ነው። ተልዕኳችን ለመጪው ትውልድ የመግባባትን ፓለቲካ በአርአያነት ማውረስ ነው። ግባችን ለፓለቲካዊ እርቅና መግባባት መሟገትና ፋና ወጊ መሆን ነው።

What is “65 percent”? 65% of Ethiopia’s population is under 24 years old. Our mission is to model a culture of political concensus for the 65%. Our goal is to advocate for, and initiate reconciliation and consensus among Ethiopians.

Post Archive